http://twondifraw.blogspot.com/

Wednesday, October 24, 2018

እዉነተኞች መምህራነ ወንጌል ዛሬ ላይ ይኖሩን?


መምህር የሚለዉ ስም ከድንጋይ ይከብዳል፡፡ በመጀመርያ ይህ ስም ወንጌል ደጋግሞ እንደሚነግረን የጌታችን የመድሀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መጠርያ ነዉ፡፡ ስለዚህ ማንኛዉም ፍጡራን ሊሸከሙት አይቻላቸዉም፡፡ ሲቀጥል ራሳቸዉን ክደዉ መስቀሉን ተሸክመዉ መድሀኔአለምን የተከተሉት የሀዋርያት መጠርያ ነዉ፡፡ በሁዋላም መናፍቃንን ድል የነሱ አንገታቸዉን ለሰይፍ የሰጡ መንበራቸዉን ትተዉ የተሰደዱት የሊቃዉንት መጠርያ ነዉ መምህር የሚለዉ ከባዱ ስም፡፡ መሬት ሲያረጅ ጃርት ያፈራል እንዲሉ ቤተክርስትያን ባታረጅም ዛሬ ዛሬ በዙርያዋ ጃርቶች መፈልፈላቸዉ አልቀረም፡፡ እናም ጃርቶች መምህራን እየተባሉ መጠራት ጀመሩ፡፡ በዚህ ዘመን በቤተክርስትያናችን አንድ ሰዉ መምህር ነኝ ብሎ በእነዮሀንስ አፈወርቅ፣ቄርሎስ፣ አትናቴዎስ፣ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በቆሙበት አዉደ ምህረት ቆሞ ለማስተማር በጉባኤያቸዉም ተቀምጦ ለማስቀጸል ቢያንስ ሁለት ነገሮችን ያሟላ መሆን ይገባዋል፡፡
1. በመምህርነት ሙያ ያስመሰከረ
2. ባይማርም በእግዚአብሄር የተመረጠ

እግዚአብሄር በማይመረመር ጥበቡ ከታናናሾች መካከል ከሚመርጠዉ መምህር ዉጭ (ይህም በደጋጎች ዘመን ነበር) በኢትዮጵያ ቤተክርስትያን መምህር ለመሆን መንገዱ አንድ ብቻ ነዉ፡፡ እርሱም ቤተክርስትያናችን ካሉዋት አራቱ ጉባኤያት ማለትም አቋቋም፣ ቅኔ፣ ዜማነና መጽሀፍ ቤት በመጨረሻዉ እርሱም በመጽሀፍ ቤት ጉባኤ ገብቶ ጠንቅቆ ተምሮ ምስጢር አደላድሎ ያስመሰከረ መሆን አለበት፡፡ ይህ ለአዉደምህረት አገልግሎት ብቻ ነዉ፡፡ በቤተክርስትያናችንም መምህር የሚባሉ ሰዎች ከሚከተሉት ሙያዎች በአንዱ፣ በሁለቱ አልያም በሁሉም ያስመሰከሩ መሆንም አለባቸዉ፡፡

የቅኔ መምህር፣የአቋቋም መምህር፣የዜማ መምህር፣የመጽሀፍ መምህር፡፡ በእነዚህ ሙያዎች ሳያስመሰክር መምህር ተብሎ በአዉደ ምህረት የሚቆም ሰዉ ትንቢቱ የተነገረበት ሰዉ ይመስላል፡፡ አንድ በቤተክርስትያን መምህር ተብሎ የሚጠራ ሰዉ ከእዉቀቱ በተጨማሪ ክህነት ሊኖረዉ ይገባል፡፡ በወንጌል በጎቼን ጠብቅ፣እንዲሁም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ ደቀመዛሙርቴ አድርጓቸዉ የተባሉት ካህናት ናቸዉና፡፡

ወደ ቀደመዉ ነገር እንመለስና አንድ በቤተክርስትያናችን መምህር የሚሆን ሰዉ ወደ መጽሀፍ ቤት ጉባኤ ከመሄዱ በፊት የሚጠበቁበት ሁለት አበይት ቁም ነገሮች አሉ፡፡ ስለ እነዚህ ቁም ነገሮችና አጠቃላይ ስለ መጽሀፍ ቤት ጉባኤ ምንነት ሳነብ ካገኘዉት መረጃዎችን ከቤተክርስትያን ሰብስቦ ጥናት የተደረገበትን የአንድ ታላቅ መጽሀፍ ዳሰሳን እንደሚከተለዉ አስፍሬዋለሁ፡፡

Two of the requirements for going to Metshaf bet are knowledge of qene and proficiency in Ge’ez. Metshaf bet has four Gubae;
1. New Testament takes 4-5 years to complete with its 35 books.
2. Old Testament takes 6-7 years to complete its 46 books
3. Book of Liqawuint takes 6-8 years
4. Books of Monks the study of the life of monks takes 3-4 years
It would take a student 19-21 years to complete Metsehafe bet. This did not include the time the student spent at Nibab Zema and Qene bet.

ከላይ እንደሚነበበዉ መምህር ተብሎ የሚሾም ሰዉ መምህር ከሚያስብለዉ መጽሀፍ ቤት ጉባኤ ከመዝለቁ በፊት ሁለቱ የሚያሟላቸዉ ቁም ነገሮች
1. ቅኔን መጠንቀቅ
2. ግእዝንም ጠንቅቆ ማወቅ ነዉ፡፡

ሙሉ ቅኔን ተምሮ ለመጨረስ ከትንሹ ባለ 2ት ስንኝ ጉባኤ ቃናን እስከ ትልቁ ባለ 12 ስንኝ እጣነ ሞገር ጠንቅቆ መማር ይጠይቀል፡፡ ባጠቃላይ ቅኔን ለመጨረስ እስከ 7 አመት እንደሚፈጅ ሀይማኖታዊ ድርሳናት ያትታሉ፡፡ ከላይ እንደተገለጸዉ በመጽሀፍ ቤት አራት ጉባኤያት አሉ፡፡ አንድ መምሀር ቢችል ሙሉዉን መማር አለበት፡፡ እርሱም አራት አይና ተብሎ ለቤተክርስትያን በሁሉም የሙያ መስክ የሚጠመድ በሬ ይሆናል፡፡ ካልሆነም ቢያንስ አንዱን ጉባኤ መጠንቀቅ አለበት፡፡ አንድ በአንድ እንይ፡፡

መጽሀፈ አዲሳት፡ የሀዲሳት መምህር ለመሆን ከ4-5 አመት መማር አለበት፡፡ በዚህም ቆይታዉ 35 መጽሀፍትን ተምሮ ይጠነቅቅና ለሀዲሳቱ አንገቱን አስከመስጠት ተጠያቂና ምስክር ይሆናል፡፡ ይህን ጠንቅቆ አስመስካሪዉ መምህሩ መምህር ብሎ ሲሾመዉ ያስመሰከረበትን ሙያ የሚገልጽ ማእረግ አብሮ ይሰጠዋል፡፡ መጋቢ ሀዲስ የሚል፡፡ መምህሩ ግን ያፈራዉን እዉቀት በህይወት/በተግባር መኖሩን ገና ሳያዉቅ በዚህ ማእረግ ቢገባዉም እንኩዋን ሊጠራበት አይወድም፡፡

መጽሀፈ ብሉያት፡ አንድ ሰዉ የብሉያት መምህር ለመሆን ከ6-7 አመት በጉባኤ መማር አለበት፡፡ በዚህም ቆይታዉ 46 መጽሀፍትን ተምሮ ሚስጥራትን ጠንቅቆ ይወጣል፡፡ እንደሀዲሳቱ ሁሉ ለብሉዩም መምህር የሙያ ማእረግ መጋቢ ብሉያት ተብሎ ያስመሰክራል

መጽሀፈ ሊቃዉንት፡ ስለእቅበተ ሀይማኖት፣ ዶግማ መምህር ለመሆን ከ6-8 አመት ይማራል፡፡ በዚህም ሀይማኖተ አበዉን፣ የእነቅዱስ ቄርሎስ፣ አትናትዮስ፣ ባስልዮስ ጎርጎርዮስ ዮሀንስ አፈወርቅ፣ ኤፍሬምና ሌሎች ታላቅ አባቶችን ድርሳን ይጠነቅቃል፡፡ በተጨማሪም ፍትሀ ነገስቱን ባህረ ሀሳቡን ፌሳሎጎስን (ስለ እንስሳትና እጽዋት የሚያጠና) ያስሄዳል፡፡ ሲጠነቅቅም ሊቀሊቃዉንት በሚል የማእረግ ስም ያስመሰክራል፡፡

መጽሀፈ መነኮሳት፡ አንድ የመጽሀፈ መነኮሳት መምህር የሚሆን ሰዉ ከ3-4 አመት በጉባኤ መማር አለበት በዚህም ቆይታዉ ሶስቱን መጽህፈ መነኮሳት ይጠነቅቃል፡፡
በአጠቃላይ ከእግዚአብሄር በታች ለቤተክርስትያን ዋልታ እና መከታ የሚሆን አንድ ሰዉ በመጀመርያ ለጌታችን ቀጥሎ ለሀዋርያቱ የተሰጠዉን ሊሸከሙት የማይቻለዉን ከባዱን ስም ‘’መምህር’’ን ለመሸከም ከ19-21 ዓመት መማር አለበት፡፡ ይህም አስቀድሞ ቅኔን ለመማር የሚፈጀዉን 7 አመት ሳንጨምር ነዉ፡፡

የዛሬ መምህሮቻችን በእዉኑ መምህራነ ወንጌል ናቸዉን?
ይህን የምንመዝነዉ በእኛ አእምሮ ያይደለ በመጽሀፍት መለኪያነት ነዉ፡፡ መጽሀፍት በቤተክርስትያናችን አንድ ሰዉ መምህር እንዴት እንደሚሆንም ሲማር የት በማን ሲማር እንደሆነ ጠንቅቀዉ ያስረዳሉ፡፡ በእነዚህ ሚዛንነት የዛሬ መምህሮቻችንን ብንለካቸዉ ምን ይመስሉ ይሆን፡፡

ዛሬ ላይ ቴዎሎጂ የሚባል ዘመናዊ ት/ትቤት ተከፍቱዋል፡፡ በእዉነቱ እነዚህ ት/ትቤቶች ኢትዮጲያዊ ትዉፊትን የጠበቁ እዉነተኛ መምህሮቻችንን ያስገኝልናልን? በመጽሀፉ መሰረት በመጽሀፍ ጉባኤ ቤት የተማሩት መምህሮቻችን ጥሬ አልያም ኮቸሮ እየቆረጠሙ ከአለም ተለይተዉ በጾምና በጸሎት ተጠምደዉ ነዉ፡፡ በቲዎሎጂ ዘመናዊ ት/ትቤት የተማሩት ደግሞ በኤክስቴንሽን ነዉ የተማሩት፡፡ እርሱም በአለም ስራቸዉ ሀጥያትም ይሁን ጽድቅ ሲወጡ ሲወርዱ ቆይተዉ በትርፍ ጊዜያቸዉ የሚማሩት ነዉ፡፡ መለኮታዊዉን የእግዚአብሄር ቃል ተምሮ መምህር ሆኖ ለማስተማር ተበልቶ ተጠጥቶ ሆድ ሲሞላ ደረት ሲቀላ የሚያስተምር ቴዎሎጂ እዉነተኛ መምህራንን ያፈራ ይሆን፡፡ መምህሮቻቸዉም በነጻ የሰጠዋችሁን በነጻ ስጡ የሚለዉን ቃል ንቀዉ በገንዘብ በደሞዝ አይደለምን የሚያስተምሩት፡፡ ተማሪዉም የእግዚአብሄርን ቃል በገንዘብ ይገዛል፡፡ ሲመረቁም ገንዘባቸዉን ለማስመለስ ይመስላል መጽሀፍ ጻፍን ብለዉ፣ ካሴት አሳተምን በማለት ቀጥታ ወደ ንግዱ ይገባሉ፡፡ ለዛዉም የእግዚአብሄርን ቃል፡፡ በኒህ ተማሪዎች አልፈርድባቸዉም፡፡ መምህሮቻቸዉ ያሳዩዋቸዉን ነዉና የተከተሉት፡፡ ቀድሞ መልካም መምህር መምረጥ ግዴታቸዉ ነበረርና ከመጠየቅ ግን አይድኑም፡፡

ሁሉም ይሁን ሆኗልም ቤተክርስትያንን የሚያሳፍራት ግን መምህር ተብለዉ ሲጠሩ፣ ተጠርተዉም በአዉደምህረት ሲቆሙ እነሱም ይገባናል ብለዉ ሲቀበሉት ነዉ፡፡ እንደእዉነተኞች መምህራኖቻችን ቅኔን ጠንቅቀዉ ይሆን፣ ግእዙ ገብቱዋቸዉ ይሆን፣ እሽ የየትኛዉስ መጸሀፍ መምህር ናቸዉ፡፡ የሀዲስ፣የብሉይ፣የሊቃዉንት፣የመነኮሳት፣የአቋቋም፣የቅኔ፣የዜማ፣በእነዚህ ጉባኤያት ስንት አመት ተማሩ፡፡ መልሱ አልቦ ነዉ፡፡ የአንዱም ስላልሆኑ ሲያስተምሩ ካስተዋላችሁ ርእሱ ከአንዱ መጽሀፍ ተመርጦ ሳለ የማይነካኩት ጥቅስ፣የማይዳስሱት መጽሀፍ የለም፡፡ ትምህርታቸዉም እንደአለማዉያን ሁሉ እዉቀታቸዉን እንጅ ህይወታቸዉን አይደለም የሚገልጸዉ፡፡ እዉቀት የተማረ ምእመን ደግሞ ምን እንደሚመስል አቡነ ሽኖዳ እንዲህ ብለዉናል፡፡ የሚያስተምርህ መምህር እዉቀቱን ከሆነ ሊቅ ትሆናለህ ህይወቱን ከሆነ ደግሞ ክርስትያን ትሆናለህ ይላል፡፡ ለነገሩ የዛሬ ዘመንም ምእመን እዉቀት ስለሆነ የሚሻ ሰይጣን አመቻችቶለታል፡፡ ለምእመኑስ እንደ አርዮስ ሊቅ ሆኖ ሲኦል ከመወርድ እንደ አላዛር ድሀ ሆኖ በአብርሀም እቅፍ መኖር ለዉድድር ሚቀርብ ሀሳብ ይሆንን
የዛሬ መምህሮቻችን የትኛዉን መጻፍ እንዳስመሰከሩና የየትኛዉ መምህር እንደሆኑ ቢለዩልን ምናለ፡፡ ስንት አመት ተምረዉ ነዉ ከየትኛዉ ጉባኤና መምህርስ አስመስክረዉ ነዉ ግሱን፣እርባታቸዉን፣ሰዋሰዉን ጠንቅቀዉ ሳይሆን መጋቢ ሀዲስ፣መጋቢ ብሉይ ወዘተረፈ የሚባሉት፡፡

በኋለኛዉ ዘመን ሀሰተኞች መምህራኖች ይነሳሉ ያለን ትንቢት እነዚህ መምህሮቻችን ሳይሆን ይቀራልን፡፡ እዉነተኛ መምህራን ላለመሆናቸዉ ግብራቸዉ ይናገርባቸዋል እኮ፡፡እንዴት
• እዉነተኛ መምህር የጌታን ወንጌል ላልተዳረሱት ለአረማዉያን አስተምሮ የስላሴን ልጅነት ያሰጣል ካልተቀበሉት ተወግሮ ሰማእትነተን ይቀበላል፡፡ እኛ ግን ካሉን ብዙ መምህር ተብየወቻችን አንዱንም አርያ ሆኖን አላየንም፡፡ የዛሬ መምህር ተብየዎቻችን አዉደ ምህረት ወጥቶ የሌሎችን እምነት ከመንቀፍ በቀር አንድም መምህር በራሱ ተመርቶ እንደ ሀዋርያት እና ሊቃዉንት አባቶቻችን በሚነቅፋቸዉ ሰዎች ጉባኤ ተገኝቶ እስላሙን ያስተማረ ጴንጤዉን እየሰበከ ብሎም የመለሰ የለም፡፡ በእኛዉ በዘመናችን እንኳ እነአያሌዉ ታምሩ አህዛብን እዉነት ካመኑበት ለምን አንነጋገርም እያሉ እዉነተኛ መምህርነታቸዉን ባስመሰከሩበት አዉደ ምህረት ዛሬ ቡችሎች ይፈነጩበታል፡፡
• እኒህ መምህሮቻችን ጩኸታቸዉ ሁሉ አዉደምህረት ላይ ነዉ፡፡ እዚህ ቦታ ላይ ደግሞ የጸኑ ክርስትያኖች ናቸዉ ያሉት፡፡ ጩኸታቸዉም ፍሬ አልባ ከመሆኑ የተነሳ አንዳቸም ሊያድን አልቻለም ጭራሽ ምእመናኑን ከማደንዘዝ ዉጭ፡፡ እስኪ ማን ነዉ በእነሱ ተምሮ አለምን ንቆ የመነነዉ፣ ማንነዉ የመነኮሰዉ፣ በእነሱ የተማረ ሰዉ ሀሜተኛ፣ዉሸታም፣አደለም ጠላቱን ወንድሙን የሚጠላ በመቃሙና በማጨሱ የቀጠለ አይደለም የሆኑት፡፡
• ለእናንተስ ምንም አይኑራችሁ የተባሉት መምህራን ወንጌልን በብር (በዉሎ አበል) ያስተምራሉ፡፡ ለማደርያቸዉ የተመቼ ሆቴል ለምግባቸዉ የላመ የጣመ ይጠይቃሉ፡፡ በእዉኑ መምህራኖቻን ከምእመናኑ ይለያሉን፡፡ እንዴት የጳዉሎስና የጴጥሮስ በረከት ሊያድርባቸዉ ይችላል፡፡

ጌታስ እናንተ ግን መምህር ተብላችሁ አትጠሩ፤ መምህራችሁ አንድ ስለሆነ እናንተም ሁላችሁ ወንድማማች ናችሁ ማቴ 23፡8፡፡ የዛሬ ሰባክያን አቤት መምህር ተብለዉ ሲጠሩ የሚሰማቸዉ ፍስሃ አቤት ደስታቸዉ፡፡

5/5/2009

Friday, October 19, 2018

ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል

አባባል ትልቅ ሀብት ነዉ፡፡ ሰዉን በአጭር መንገድ ቶሎ ያግባባል፡፡ አብዛኛዎች አባባሎች ሲወርዱ ሲዋረዱ የመጡ ናቸዉና ትዉፊታቸዉን ጠብቀዉ ሊሄዱ መልእክታቸዉ ሳይዛባ ሊነገሩና ሊጠበቁ ይገባል፡፡ አንዳንዴ ግን አንዳንድ አባባሎችን ትክክለኛዉን መልእክታቸዉን ገልብጠን ስንረዳቸዉና ስንጠቀምባቸዉ ይስተዋላል፡፡ ከእነዚህ ትክክለኛ  መልእክታቸዉ ተገልብጦ ከሚነገሩ አባባሎች መካከል አንዱ ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀድዶ ይሰፋል ነዉ፡፡ ይህ አባባል የምንኩስና ህይወትን በተመለከተ የሚነገር ነዉ፡፡ምንኩስና የሰዉን ልጅ ከሰማያዉያን መላእክት ጋር አንድ የሚያደርግ በፈቃድ የሚቀበሉት ታለቅ ተጋድሎ ያለበት ክብር ነዉ፡፡ ከመላእክት ጋር የሚያመሳስለዉም አንድ በምንኩስና ህይወት ዉስጥ ያለ ሰዉ የዘወትር ስራዉ እስከ ጊዜ ጥሪዉ ድርስ እንደመላእክቱ 24 ሰዓት በጾም በጸሎትና በምስጋና ፈጣሪዉን ማገልገል ብቻ ስለሆነ ነዉ፡፡ፕሮፌሰር ጌታቸዉ ሀይሌ በደቂቀ እስጢፋኖስ መጽሀፋቸዉ ገጽ 64 የህዳግ ማስታወሻቸዉ ላይ ስለ ምንኩስና ያሰፈሩትን እንይ፡፡

አንድ ሊመነኩስ የፈቀደ ሰዉ መጀመርያ በፈቃዱ ከአለም መለየቱን ከዚያም የምንኩስና ኑሮዉ ምን እንደሚመስል የሚያስረዳ ጽሁፍ ያነቡለታል፡፡ በእግዚአብሄርና በሰዉ ፊት ድምጹን ከፍ አድርጎ ሲስማማ ከፊታቸዉ ያጋድሙትና የጠጉር ልጪት፣ ቀጥሎ ለምንኩስናዉ በሚሆን ልብሱ በሰዉየዉም ላይ እንደሞተ ሰዉ ጸሎተ ፍትሀት ይጸልያሉ፡፡ ከዚያ በሁኋላ መጀመርያ መምህሩ (የገዳሙ አበምኔት) ቀጥሎ በፍትሀቱ የተካፈለዉ ሁሉ ይባርከዉና ያለብሱታል፡፡ የመጨረሻዉ ጸሎት ተጸልዮለት የምንኩስናዉን ህይወት ይጀምራል፡፡ እንደህጉ ቢሆን ከጥቂት አመታት በኋላ ደግሞ አስኬማ የሚባል ልዩ ልብስ ይሰጠዉና ወደ ከፍተኛዉ ደረጃ ይሻገራል፡፡ አስኬማ ከነት የሚሰራ 12 የመስቀል ምልክት ያለበት ቆዳ ነዉ፡፡ እንደ ህጉ ቢሆን ከአስኬማ በኋላ መነኩሴ ከገዳም አይወጣም፡፡ የመጀመርያዉን አስኬማ ለመጀመርያዉ መነኩሴ ለአባ እንጦንስ የሰጠዉ መልአኩ ስለሆነ ልብሱ አስኬማ መላአክት (የመላክት ልብስ) ይባላል፡፡ መነኮሳቱም የምድር ላይ መላአክት ይባላሉ፡፡ አሁን ግን የመነኮሳቱን ልብስ አስኬማ ይሉታል፡፡

ምንኩስና የክብሩን ያህል ጋሩም እጅግ ብዙ ነዉ፡፡ አሁን ማተኮር የሚያሻዉ ጋሩ ወይም መከራዉ ላይ ነዉ፡፡ ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል የሚለዉ አባባል የምንኩስናጋሩን የሚያሳይ ትክክለኛ ኢትዮጵያዊ ቢሂል ስለሆነ ጋሩን ስንተነትን ብሂሉ ምን እንደሆነ በደንብ ይገባናል፡፡አንዳንድ ሰዎች ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል ሲባል መነኩሴ ስራ ስለሌለዉ ዝም ብሎ ቁጭ ከሚል ቆቡን ቀዶ መስፋት የሚወድ የሚመስላቸዉ አሉ፡፡ አባባሉ የሚነገረዉ ግን በተቃራኒዉ ስራ ለበዛበት እና ባተሌ ለሆነ መነኩሴ ነዉ፡፡ እንዴት እንደሆነ በዝርዝር እንይ፡፡ አንድ መነኩሴ በማህበር በገዳም ወይም በተባትሆ በበርሀ ሲኖር ህይወቱ በሙሉ ለ24 ሰዓት ምስጋና የተሰጠች ናት፡፡ ይህም የምስጋና ህይወት መነኮሱ በግሉ ከአመት እስከ አመት የሚደረሱ የ7 ሰዓት የእየለቱ ጸሎቶችን ይይዛል፡፡ ህይወቱ ዘወትር በዚህ የተጠመደቸ ናት፡፡ በማህበርም ከአመት እስከ አመት የማይታጎለዉ ቅዳሴዉ፣ ኪዳኑ፣ ማህሌቱ፣ ሰአታቱ ሌላኛዉ የምስጋና ህይወት ነዉ፡፡ ከምስጋና ህይወት በተጨማሪ የአንድ መነኮስ ህይወት እድሜ ዘመኑን በስራ የተጠመደች ናት፡፡ በገዳም ያለ መነኩሴ ቅዱሳት መጽሀፍትን ዘወትር ማንበብ ይጠበቅበታል፡፡ መጽሀፈ መነኮሳትን፣ መጽሀፍ ቅዱስን፣ ገድላትን ተአምራትን ያነባል ይተረጉማል፡፡ በእኛ ሀገር በተለይ የመነኮሳት ስራ እጅግ የበረታ እንደነበር የቅዱሳን አባቶቻችንን ገድል ማየት እንችላለን፡፡ በመካከለኛዉ ዘመን የነበሩ መነኮሳት ከአንድ ጉባኤ ትምህርት ሲጨርሱ እንደዛሬዉ በቃል ብቻ ማስመስከር አይጠበቅባቸዉም፡፡ ይልቁንም በቃል ያስመሰከሩትን ትምህርት ብራና ፍቀዉ፣ ሌጦ አዘጋጅተዉ ይደጉሱና ብእር ቀርጸዉ የብራና ጽሁፍ ያዘጋጃሉ፡፡ ለዚህ ነበር የመነኮሳት መፍለቅያ የነበረዉ የአባ ኢየሱስ ሞአ ገዳም የኢትዮጵያ የስነ መለኮት ዩንቨርስቲ የሚባለዉ፡፡ እኒህ መነኮሳት ከዚህ በኋላ ለሌላ ትልቅ ተጋድሎ ራሳቸዉን ያዘጋጃሉ፡፡ እግዚአብሄር በፈቀደላቸዉ ገዳም ሲኖሩ የዘወትር መንፈሳዊ ስራዎቻቸዉን ከፈጸሙ በኋላ ፍጹም ተዋርዶና ትህትና ድካምንም ለሚጠይቅ የጉልበት አገልግሎት ይሯሯጣሉ፡፡

እንበለ ስጋ ኢትቀዉም ነፍስ ነዉና መጽሀፉ የሚለዉ መነኮሳት ለስጋቸዉ መጠገኛ ለሚመገቡዋት ትንሽ /ኩርማን ዳቤ ብዙ ይደክማሉ፡፡ ለዚህም አንድ የገዳም ረድ የሆነ መነኩሴ ዳቤ የሚጋገረዉን እህል በእጅ ወፍጮ ይፈጫል፡፡ ወፍጮ የሚፈጨዉ ተጎንብሶ ስለሆነ በስግደት የደከመን ወገብና የእጅ መገጣጠምያ እጅግ ይፈትናል፡፡ የፈጨዉን ዱቄት ያቦካል ይጋግራል፡፡ ከወንዝም ወርዶ ዉሃ በማሰሮ ቀድቶ በትክሻዉ ተሸክሞ ያመላልሳል፡፡ ይህ መነኮስ ዳቤዉን ከመጋገሩ በፊት ማገዶ ያስፈልገዋልና ወደ በርሃ በመዉረድ እንጨት ቆርጦ ፈልጦ ተሸክሞ ለገዳሙ ማምጣት አለበት፡፡ የፈለጠዉን እንጨት ማገዶ በጢሱም በእሳቱም እየተገረፈ መነኮሳትን አብስሎ ይመግባል፡፡ ከዚያም ለመቅደሱ ዉስጥ አገልግሎት የሚሆ ነገሮችን በማዘጋጀት ጣሩና ጋሩ ይቀጥላል፡፡ ግብር ያደቃል፣ ህብስቱን ይጋግራል፣ ወይኑን ይጠምቃል፣ ፍህም ያያይዛል፡፡ ከዚህ ድካም ሁሉ በኋላ ወደ ህያዉና እዉነተኛዉ ሰማያዊዉ አገልግሎት ይመለሳል፡፡ በትህትናና በለቅሶ በአንቃዶ ህሊና ቅድመ እግዚአብሄር ቁሞ እግሩን ሳያጥፍ ይቀድሳል፣ ያወድሳል፣ ይጸልያል፡፡ ከጸሎት ቀጥሎ ወዙ እስኪንጠፈጠፈ ጣቶቹና ጉልበቶቹ እዥ እስኪወርዳቸዉ ድረስ ይሰግዳል፡፡ ለድካመ ስጋዉ አረፍ ባለበትም ቅዱሳት መጽሀፍትን ያነባል፡፡

ይህ ምድራዊ መልአክ መነኩሴ አደለም የእረፍት ሰዓት ማግኘት ቀርቶ ስለረፍት እንኳን የሚያስብበት ጊዜ የለዉም፡፡ ሆኖም ግን ስራዉን በጊዜ ጨርሶ ምንም የሚሰራ ስራ ጠፍቶ መነኩሴዉ እንደሚቦዝን ቀድሞ ካወቀ ከላይ ያልነዉ የኢትዮጵያዉያንን አባባል ስራ ላይ ያዉላል፡፡ መነኩሴዉ ቆቡን ቀዶ መስፋት ይጀምራል፡፡ ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል ማለት ቆብን ቀዶ መስፋት ለመነኩሴ ስራ ሆኖ ሳይሆን እራስን ከዝርዉነት ለመጠበቅ የሚያደርገዉ ሌላኛዉ የመንፈሳዊ ተጋድሎ ክፍል ነዉ፡፡ ይህ ደግሞ ሰዉ ሰራሽ ህግ ሳይሆን ከፈጣሪ የተሰጠ ራስን ከፈተና የመታደጊያ መንገድ ነዉ፡፡ በግብጽ በርሃ ይኖር የነበረዉ የመጀመርያዉ ባህታዊ አባ ጳዉሊ ከፈጣሪዉ ይህ ስራ ተሰጥቶታል፡፡ አባ ጳዉሊ በብህትዉና ሲኖር ሌትም ቀንም አምላኩን እያመሰገነ በትግሀ ጸሎት ነበር፡፡ አባ ጳዉሊ ጸሎት አድርሶ ሲጨርስና አእምሮዉ ሲያርፍ ሰይጣን የአለምን ሀሳብ እያመጣ ጥሎት የመጣዉን ከንቱ ህይወት እያሳሰበ እንዳይፈትነዉ እግዚአብሄር መለአኩን ይልክለታል፡፡ መለአኩም ይመጣና ከበርሀ የበቀሉትን የዘንባባ ቅጠል እየፈተለ ምንጣፍ እየሰራ ያሳየዋል፡፡ ከዚህ በኋላ አባ ጳዉሊ ከጸሎት በኋላ ስራ ሳይፈታ ሁሌም የዘንባባ ቅጠል በመጠቅለል ምንጣፍ ይሰራ ነበር፡፡ ልብሱም በእለተ እረፍቱ አካባቢ ከቅዱስ እንጦስ ጋር ተገናኝቶ የኮፕት መነኮሳት ልብስ የሆነዉንና አባ ጳዉሊም የኮፕት ቤ/ክ ስርአት ተገዥ መሆኑን ለማስመስከር  ምልክት ይሆነዉ ዘነድ የምንኩስናን ልብስ ከእንጦንስ እስኪቀበል ድረስ ከቅጠል የተሰራ ቀሚስ ነበር፡፡

ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል የሚለዉ ብሂል ለስራ አጥ መነኩሴ ወይም መነኩሴ ስራ የለዉም ለማለት የነተነገረ የሚመስለን ሰዎች ካለን አሁን በእኛ ዘመን ከምናየዉ ሁናቴ የአንዳንድ መነኩሴ ሳይሆኑ ግን መስለዉ ከሚኖሩ ሰዎች እየተነሳን ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም  ዛሬ ላይ እንኳን ቆቡን ቀዶ የሚሰፋ ትጉህ መነኩሴ የተሰፋ ቆብ በትክክል የሚያደርግ መነኩሴ የለም፡፡ በትክክል የሚያደርግ ስል ሳያዛንፍ ማለቴ እንዳልሆነና የምንኩስና ቆብ ትርጉሙን በትክክል የተረዳ፣ ከነማን እንደተጫነለትና ለምን እንደተጫነለት ማለቴ ነዉ፡፡ በመካከለኛዉ ዘመን የነበሩ ኢትዮጵያዉያን መነኮሳት እኮ ሲመነኩሱ ብዙ ዉጣ ዉረድ የሚያስጉዝ መንገድ ካለበት ገዳም የሚኖር አባት አፈላልገዉ ሄደዉ ይቀበላሉ፡፡ ለዛዉም ይገባኛል ብለዉ ሳይሆን በአባቶች ተገፋፍተዉ አልያ አምላካቸዉ በራእይ ነግሯቸዉ ነዉ፡፡ አስኬማዉን እና ቅንዋቱን  ደግሞ ከሌላ ተጋድሎ በኋላ እንዲሁ አምላክ ከፈቀደላቸዉ አባት በትህትናና ራስን በማዋረድ እጅ ነስተዉ ይቀበላሉ፡፡ ዛሬ ምንኩስናን አንድ ሰዉ እንዴት ይሆን የሚቀበለዉ? በመካከለኛዉ ዘመን ይኖር የነበረዉ አባ እስጢፋኖስ እንዲህ እንደዛሬዉ ዘመን ምኩስናን ተቀብለዉ በህጉና በስርአቱ ያልተጉዋዙትን አባቶች ነን የሚሉትን እንዲህ ገስጾዋቸዋል፡፡

እነሱስ ቢሆኑ ራሳቸዉን ለአባቶቻቸን ለቅዱሳን ሐዋርያትና ተከታዮቻቸዉ ለመነኮሳት አባቶች ለእንጦንዮስና ለመቃርዮስ ትእዛዝ ሳያስገዙ የአባትነት ስም እንዴት ወለዱ?  እዉነትን የሚፈልገዉን በከንቱ የሚቃወሙ ከሆነ እኔ ደግሞ ወይ የእግዚአብሄር ወይ የእግዚአብሄር ባሮች ሁኑ እላቸዋለሁ፡፡
ዛሬም በዘመናችን የቤተክርስትያን ዘቦች ይሆናሉ ተብለዉ አለምን ንቀናል ምድራዊ መለአክ ሆነናል ብለዉ የመነኮሱ ሰዎች በስልጣንና በነዋይ ጥም ተነድፈዉ እዉነት ፈላጊ የዋህ ምእመናንን ከመንገድ ሲያስወጡ የቤቴክርስትያንን ህግና ቀኖነዋን ሲንዱ ይገኛሉ፡፡ ታድያ ያ አባባል ለእንዲህ አይነት መነኩሴዎች የተነገረ አይደለም፡፡ እንዲህ አይነት ስራ ፈት መነኮሳት በበዙበት ዘመን እማ ብሂሉ ሊሆን የሚችለዉ፡፡
ቆቡን ቀዶ የሚሰፋ፣
መነኩሴ  እኮ ዛሬ ጠፋ፡፡