http://twondifraw.blogspot.com/

Monday, June 1, 2020

ያልተዘመረለት



በአርሶ አደሩ ማህበረሰብ ዉስጥ ሲጠሩት አቤት ሲልኩት ወዴትን በተግባር ከትህትና ጋር የሚያሳይ ትጋቱ ከንብ ጋር የሚስተካከል አንድ ወሳኝ የሆነ አካል አለ፡፡ ይህ አካል በስራ ትጋት ብቻ ሳይሆን በስነ-ግጥም በአካባቢያዊ አባባሎች፣ በሽለላ እና ቀረርቶ በአጠቃላይ በስነ-ቃል ችሎታዉ ጎልቶ ይታወቃል፡፡ ቀን ሲሰራዉ የዋለዉን፣ ወደ ፊት ሊሰራ ያሰበዉን፣ ሀላፊዉንና መጻኢዉን ኩነቶች እያነሳ ዱሩን፣ ሸንተረሩን፣ ጉሙን፣ ጎርፉን፣ አእዋፉን፣ ሰብሉን፣ አበባዉንና እሸቱን በዜማ እየነካካ በፉጨት እያማለለ በዋሽንት እያታለለ የሀገሬዉን ሰዎች ያዝናናል የቀዘቀዘዉን መንደር ያሞቃል፡፡ ይህ አካል ታድያ በግብር ስሙ እረኛ ይባላል፡፡ እረኛዉ በቀየዉ ሲኖር ከሚታወቅባቸዉ አበይት ስራዎቹ መካከል አቃቢነት ነዉ፡፡ አቃቢ ማለት ጠባቂ ሲሆን እረኛዉ ከሁሉም ነገር ሰብልን እና ከብቶችን በመጠበቅ ግብሩ ይታወቃል፡፡ ሰብሉን ሲጠብቅ ታድያ ተግቶና ታጥቆ ነዉና አስቀድሞ ለወፉ ወንጭፍ ለከብቱ ጅራፍ ፈትሎ ያዘጋጃል፡፡ ቀጥሎ ከሰብሉ መሬት መሃል ወይም ዳር ላይ ማማ ይሰራል፡፡ ከሰራዉ ማማ ራስ ላይ በኩራት ቆሞ እየተጎማለለ የሰበሰበዉን ጠጠር በወንጭፍ አሽከርክሮ በመወርወር በበልግ የዘራዉን ማሽላዉን፣ ገብሱን፣ በቆሎዉንና ስንዴዉን በመኸር ወቅት ከማማዉ ላይ ቆሞ በአራቱም ማእዘን እየተዘዋወረ ተግቶ ይጠብቃል፡፡ ከዝንጀሮዉ፣ ከፍልፈሉና ከአእዋፋቱ ጋር ሲፋለም ሌሊት ወጥቶ ሌሊት ይገባል፡፡ ይህ አቃቢነቱ ሰብሉ እስኪጎመራ ብሎም እስኪደርቅ ድረስ ይዘልቃል፡፡
ሌላኛዉ የእረኛዉ አቃቢነት ደግሞ ከብቶቹን መጠበቅ ነዉ፡፡ ቆየት ባሉት ዘመናት እረኛ ከብቶቹን የሚያረባዉ ደጋማዉን ቀየዉን ለቅቆ በመሄድ በርሀ ወርዶ  ጎጆ በመቀለስ ነበር፡፡ ይህ ዘዴ በአካባቢዉ ህብረተሰብ ዘንድ ደረባ በመባል ይታወቃል፡፡ በደረባ ጊዜ እረኛዉ የሚያርሱ በሬዎችን ከደጋዉ ትቶ ላሞችን እና ጊደሮችን ከነጥጆቻቸዉ ይዞ ለሰዉ ልጅ ሳይቀር የሚያጓጓዉን ረጃጅም እና ወዛም ሳር ለመመገብ በርሀ ወርዶ ይከትማል፡፡ ከዚያም በጨፈቃ የተገደገደች ጊዚያዊ ጎጆ ከበርሃዉ እሾሀማ እንጨቶች ለቅሞ ይቀልሳል፡፡ የበርሃው ተናካሽ ፍጡራን ስለሚያስቸግሩት ለመኝታዉ ከመሬት ከፍ አድርጎ በባላ ላይ ጠንካራ እንጨቶችን ሰካክቶ ቆጥ ይሰራል፡፡ ጊዜያዊ መኖርያዉን ከበርሃ ያደረገው እረኛ ከወር አንድ ወይም ሁለት ጊዜ ወደ ደጋዉ ብቅ እያለ ዘመድ ይጠይቅና የእለት ስንቅ አስበስሎ በአገልግሉ አንግቶ ዉኃ በቅል ይዞ ሲያሻዉ በፉጨት ሲፈልግ በድምጽ አባት አደር በሆኑ ዜማዎች ቅራርቶዉንም ዘፈኑንም ልብን በሚሰርቅ ሁናቴ እያንጎራጎረ ይመለሳል፡፡ ወደ ደጋዉ ሲወጣ ለዘመደቹ ለእርሻ እና ሌሎች ስራ የሚዉል የበርሃዉን ሲሳይ ለጎጆ ቤት ክዳን የሚሆን ፊላ የተባለዉን ሳር፣ ለሽማግሌዎች ምርኩዝ የሚሆን ትለም ከተባለ ዛፍ የተዘጋጀ ሽመል፣ የምሳር እጀታ፣ የጅራፍ ልጥ፣ ቀበርቾ፣ ድግር እና ሌሎች ማለፍያ ሲሳይ ተሸክሞ ከደጋዉ ይዘልቃል፡፡ እረኛዉ በበርሀ ህይወቱ ማታ እሳቱን እያነደደ ዋሽንቱን እየነፋ ሌሊቱን ያዋግድና ከቆጡ ገብቶ ጋደም ይላል፡፡ የሌሊት አዉሬዎች በተለይ ነብርና ጅብ ከብቶቹን እንዳይተናኮሉበት ከመኝታዉ በዉድቅቱ ሌሊት ደጋግሞ እየተነሳ ይሰልላል፡፡
እረኛዉ ከቤቱ በራቀ ወቅት ስንቁን የሚያገኘዉ ደጋ ሲሆን ከሰብሉ ገብቶ እሸቱን በርሀ ሲዉል ደግሞ ከበረት ገብቶ ወተቱን በማማረጥ እና በመሸምጠጥ ነዉ፡፡ እሸቱን በሁለት መንገድ ይመገባል፡፡ የመጀመርያዉ ጥሬዉን ምንም ማብሰል ሳያስፈልገዉ ስንዴና ገብስ ከሆነ የእሸቱን ምርቅ በጥፍሮቹ ነቅሎ አስወግዶ በመዳፎቹ እያሸ ባቄላና አተር ከሆነም ቦጥቡጦ በኪሱ ከቶ አልያም በፎጣው ታቅፎ እየፈለፈለ ይቅማል፡፡ ሁለተኛዉ ደግሞ ሁሉን የእሸት አይነት በእሳት በማብሰል በቆሎ ከሆነ ጠብሶ ስንዴ ከሆነ ደግሞ አንኩቶ ነዉ፡፡ ድርቅ በሆነ ዘመን እረኛዉ ታላቅ ስደት ከደጋዉም ከበርሀዉም ይገጥመዋል፡፡ እንደ ደጉ ዘመን ለምለም እሸትና ትኩስ ወተት ማግኘት የዉሀ ሽታ ይሆንበታል፡፡ በእንዲህ አይነት ክፉ ዘመን የነበረን እረኛ ገጠመኝ አልያም ታሪክ እንደሚከተለዉ ተደርሶለታል፡፡

አልቦ ወተት
አልቦ ወተት ከላሚቷ፣
እረኛዋ ሊጠጣ ሲያመነታ፣
ሙጃ አብልቶ ጨዉ አልሶ፣
እጅ ነስቶ ተጎንብሶ፣
የአጋተ ጡትዋ ቢያስመኘዉ፣
እረኛዉ ወተት ወተት አሰኘዉ፡፡
ቅሉን ለግቶ እግሩዋን ግዶ፣
እምቦሳዋን ግጭ ገብቶ ከጥባት አስጥሎ አናዶ፣
ከግርዋ መሃል ተቆጥጦ፣
አይኑን ጋትዋ ጫፍ ላይ አፍጥጦ፣
በጣቶቹ አድፈጥፍጦ፣
አፍረጥርጦ ንጦ፣
ግጩን ለቆ ግድዋን ፈትቶ፣
ከደረባዉ ጎጆዉ ገብቶ፣
ከቆጧ ላይ ዘሎ ወጥቶ፣
ጉምጁ እረኛ ሊጠጣ፣
ቅሉን ይዞ አንጋጠጣ፡፡
አይ ክፉ እድል የድርቅ እጣ፣
ከደረቱ ቢሰበቅ ምላሱን ቢስብ ቢያወጣ፣
ከጉሮሮዉ የምትመጣ፣
ጠብታ እንኳን ከቅሉ አጣ፡፡
በቅል ወተት አልቦ ነበርና፣
ምን ፉት ይበል እረኛዉ አንገቱንስ ቢያቀና፡፡

ይህ ሲሳይ የራቀዉ እራብ የገረፈዉ ትጉሁ የበርሃ እረኛ በእንዲህ አይነት ጊዜ ወደሌላኛ ማግመጫዉ ወደ እሸቱ ሄዶ አምሮቱን ሊወጣ ይገደዳል፡፡ ድንቹ ከደረሰ አንካሴዉን ለበቆሎዉ እና ማሽላዉ ደግሞ ማጭዱን፤ ለአተሩና ባቄላዉ ስልቻዉን  ይዞ ከደጋዉ ይዘልቃል፡፡ ከዛም ልቡ ከፈቀደው ሆዱ ከወደደዉ ማሳ ገብቶ ፍላጎቱን አርክቶ እየፏለለ ይመለሳል፡፡
በደጋዉ አለም ከድርቅ መቅሰፍት ተርፎ ለአካለ መጠን የደረሰ አዝመራን በማዳሸት፣ በመጋጥና በማበላሸት የእረኛዉን ልፋትና ተስፋ ከአፈር ደባልቃ ከንቱ የምታደርግ እሱ ራቡን ሊገድል በሄደ ወቅት ሰብሉን ቀድማ ገድላ የምትገኝ አንድ ወፈፌ አዉሬ አለች፡፡ እርስዋም ጃርት ትባላለች፡፡ ጃርት በአንድ አካባቢ የሚገኝን የተለያዩ ገበሬዎች ሰብል ድንበር ሳያግዳት እገሌ የጌታ ዘር ነዉ ይገለኛል እገሌ ደግሞ ጭሰኛ ነዉ ምን ያመጣል ሳትል ደስ ካላት ገብታ በልታ ደስ ካላላት ደግሞ አልፋ ሌላዉ ጋ በመሄድ በአንድ ሌሊት ብዙ አዝመራ አበላሽታ ታድራለች፡፡ ይህንን አስቀድሞ የሚያውቅ እረኛ በመኸር ወቅት በጠዋት ገስግሶ ተነስቶ ወደ ማሳዉ ይሄድና የተበላ ሰብል ካለ አዝኖ ካልተበላም ተደስቶ እሸቱን እየቃመ ወደ ሰፈሩ ይመለሳል፡፡ ታድያ የስነ-ቃል ባለጸጋ ነዉና ይህን ማዘኑንና መደሰቱን ለህብረተሰቡ የሚገልጸዉ በስነ-ቃል ነው፡፡ ስነ-ቃሉ እንደየ ጉዳቱ መጠን፣ እንደየ ድርጊቱ ሁኔታ ይወሰናል፡፡
በጥያቄና መልስ መንገድ የሚቀርብ ስነ-ቃል ሲኖር  በሁለት ወይም ከዚያ በላይ ባሉ ጃርቶች መካከል የተደረገ ሌሊት የሰሩትን ጀብዱ የሚያሳይ ቃለ ምልልስ ነዉ፡፡ ይህ እረኛ ሰብሉ  የተበላበትን ወይም ሰብሉ ምንም ያልተነካበትን ገበሬ ስም እየጠቀሰ ጃርቶች ያን ሰብል ለምን እንደበሉት ወይም ደግሞ ለምን እንዳለፉት እርስ በራሳቸዉ ሲነጋገሩ እንደሰማ ሆኖ  በራሱ ጊዜ የደረሰውን እንደሚከተለዉ በጥኡም ዜማ ይተርካል፡፡
ለምሳ ጃርቶች ጌትነት የተባለ ገበሬን የበቆሎ አዝመራ በጣም በጎዱት ጊዜ
ጃርት 1 ፡ ይሄ የማነዉ በቆሎ? ስትል ትጠይቃለች
ጃርት 2 ፡ የአያ ጌትነት፡፡  በማለት ትመልስላታለች
ጃርት 1 ፡ የዛ የመልካሙ?
ጃርት 2 ፡ አዎ፡፡
ጃርት 1 ፡ ያዥዉ በመሙ[1]፡፡
ጃርቶች ሀብታሙ የተባለን አርሶ አደር ድንች ሳይበሉ አልፈዉ የሌሎችን ገበሬዎች ድንች በበሉ ጊዜ ደግሞ
ጃርት 1 ፡ ይሄ የማን ነዉ ድንች?
ጃርት 2 ፡ የአያ ሀብታሙ
ጃርት 1 ፡ የዛ የተላፋፊዉ?
ጃርት 2 ፡ አዎ
ጃርት 1 ፡ ተይዉ እለፊዉ
ጃርቶች የጌትነትን በቆሎ ለምን በጣም እንደጎዱትና የሀብታዉን ድንች ለምን እንዳለፉት እረኛው ተመራምሮ የደረሰበትን በዚህ መንገድ ለህብረተሰቡ ይገልጣል፡፡
እረኛው ከጥያቄና መልስ በተጨማሪ የጃርቶቹን ጥፋት በግጥም መልኩ ያቀርባል፡፡
አንድ ሙሉጌታ ከተባለ ገበሬ የበቆሎ ሰብል ገብታ በቆሎዉን ግጣ ጨርሳና አገዳዉን ከመሬት ጨፍጭፋ ጥላ ከፍተኛ ጉዳት ያደረሰች ጃርት እረኛዉ ሲነጋጋ ሄዶ የተበላዉን ሰብል ያይና ጃርቷ ለሰብሉ ባለቤት ማለትም ለአቶ ሙሉጌታ ምን እንዳለች በስነ-ቃል እንዲህ ብሎ ባለቤቱን ያረደዋል፡፡
ሙሉጌታ አባተ ወላንሳ ወላንሳ፣
ፍሬዉን በላዉት ገለባዉን አንሳ፡፡
ከአያ አላምር ፈለቀ ማሳ ገብታ ካለምንም ስጋት ሌሊቱን ሙሉ ድንቹን ስትግጥ አድራ ከመጠን በላይ ከመጥገቧ የተነሳ ወደ ጉድጓዷ መሄድ ተቸግራ በዛው በድንቹ መሃል ስትንጎራደድ ለተገኘችዋ ጃርት ደግሞ
አላምር ፈለቀ ቶፋ ግዛልኝ፣
ጥራጥሬው ድንች ሆዴን ጎጠረኝ፡፡
አንድ አጤ ፈንታ የምትባል ባልዋ ሞቶባት ብቻዋን የምትኖር የገበሬ ሚስት ነበረች፡፡ ሁሉንም መሬቶቿን የእኩል ሰጥታ በገበሬ እያሳረሰች ጓሮዋን ደግሞ ራሷ ታስጎልማለች፡፡ ጓሮዋን በቆሎ ታዘራና በዉስጡ ደግሞ ክረምት እህል በሚያጥርበት ሰዓት ቶሎ እንዲደርስላት ድንች፣ ቃሪያና ዱባ ራሷ ትተክላለች፡፡ ነገር ግን ያች ክፉ ጃርት ድንቹ ገና ማበብ ሲጀምር ዱባው ሲያኮረኩር በውድቅቱ ሌሊት ትገባና በቅጥ ያልደረሰውን ድንችና ዱባ ስሩን ነቅላ ግጣና ገምጣ እንዳልሆነ አድርጋ ትሄዳለች፡፡ ወ/ሮ አጤ በጠዋት ተነስታ ስትሄድ ለክፉ ቀን ይደርሱልኛል ብላ የተከለቻቸው ሰብሎች ያለ እድሜያቸው ተቀጥፈዉ ታገኛቸዋለች፡፡ ከዚያም ንዴቷና ቁጭቷ መድረሻ ሲያሳጧት እጆቿን ከፍ አድርጋ እያጨበጨበች እየየ ስትል ታረፍዳለች፡፡ ይህ ድርጊቷ በእየለቱ የተለመደ ሆነ፡፡ ይህንን ያየ እረኛ እንደሚከተለው ተቀኘላት፡፡
እመት አጤ ፈንታ ምኗን ትድራለች፣
በነጋ በነጋ ታጨበጭባለች፡፡
አንድ አንዳርጌ አሳዬ የተባለ ባለጉዛም ገበሬ ነበር፡፡ ለቁጥር የሚያታክቱ የቀንድና የጋማ ከብቶች፣ ጉረኖ የማይችላቸው በጎችና ፍየሎች ነበሩት፡፡ ፍየሎች በጣም አስቸጋሪዎች የነበሩ ሲሆኑ ወደ መሰማሪያ ሜዳ ሲሄዱ የሰው ሰብል ውስጥ ዘለው በመግባት ሜዳ ውለው ከቤት ሲመለሱ ደግሞ ከጥራጥሬው እህል ማለትም ከባቄላው፣ ሽምብራውና በቆሎው ጎተራ ላይ ተንደርድረው እየተሰቀሉ በመብላትና በማፍሰስ ጠባቂ እረኞቻቸውን በጣም ያሰቃዩ ነበር፡፡ አንዳርጌ የበቆሎ ሰብሉን በእጅጉ የጎዳችበትን ጃርት ለመግደል ንጋቱ ከተባለ ሲሶ ተካፋይ እረኛው ጋር አንድ ቀን አንድ ዘዴ ይዘይዳል፡፡ ጃርቷ ሲቀርቧት በእሾኋ ስለምትወጋ ያም ሆኖ ከጀርባዋ የፈለገ ቢመቷት ስለማትሞት ንጋቱ ጃርቷን በረጅም ዘንግ ከጀርባዋ ሆኖ እየነዳ ወደ ጉድጓዷ ስትሄድ አንዳርጌ ደግሞ ከጉድጓዷ አጠገብ ሆኖ አፍነጫዋን መትቶ ለመግደል ተስማሙ፡፡ እንዲህ እያደረጉ ብዙ ጊዜ ቢደክሙም ተሳክቶላቸው ጥቂት ጃርቶችን ሲገድሉ ብዙዎችን ግን ሊገድሏቸው አልቻሉም፡፡ በዚህ ጊዜ የቀየው እረኛ የጃርቷን ስሞታ በሚከተለው መንገድ አሰማላት፡፡
እድሌ ነው እንጅ ኮከቤ ቢሰበር፣
ካንዳርጌ ፍየሎች መች እከፋ ነበር፡፡
ንጋቱ መልካም ሰው ሲቸበችበኝ፣
አንዳርጌ ክፉ ሰው ሙጩን ጠረገኝ፡፡
ታድያ በጃርቶች መካከል የተደረገዉን የመጀመርያዉንም ቃለ ምልልስ ሁለተኛዉንም ግጥም የሚናገርበት እረኛዉ የራሱ የሆነ የሚስብና አእምሮ ዉስጥ ተቀርጾ የሚቀር የራሱ የሆነ ዉብ ዜማ አለዉ፡፡ ችግሩ ዜማውን በድምጽ ማሰማት ብቻ እንጅ በጽሁፍ ማስነበብ ስላልቻልኩ (ለቅዱስ ያሬድ በድፋት፣ ርክርክ፣ ቅናት፣ ሰረዝ …. ምልክቶች የተቻለ ለእኔ ግን አልተቻለኝም) ሙሉዉን የእረኛዉን ችሎታ እዚህ ላይ ማቅረብ አልተቻለኝም፡፡ ዜማዉን ነጥየ ስነ-ግጥሙንና ስነ-ቃሉን ብቻ ለማቅረብ ተገድጃለሁ፡፡ የዜማዉን ይዘት ምን እንደሚመስል ትንሽ ምናባዊ ምስል ለመስጠት ያህል ለማስረዳት ብሞክር ግን እንዲህ ይመስለኛል፡፡ ይህ የጃርቶችን ቃለ-ምልልስ እረኛዉ የሚያዜመዉ ቀዝቀዝ ባለ ድምጽ ሆኖ ዝግ ባለ የቃላት ፍሰት ለስለስ ባለ ዜማ በማንቆርቆር ነዉ፡፡ ከኢትዮጵያ የቅኝት ስልቶች ከየትኛዉ ሊመደብ ይችላል ብትሉኝ ከትዝታ ማይነር ቅኝት ጋር ሳይሆን እንደማይቀር እገምታለሁ፡፡በስተመጨረሻም እኔ ብዙ ታላላቅ ሰዎች ያልተዘመረለት በሚል የሬድዮ መርሀ ግብር ታሪካቸዉ ሲወሳላቸዉና ሲዘመርላቸዉ ሰምቻለሁ፡፡ ይህ እረኛ አዚሞ ዜማዉ ያልተሰማለት እና ተናግሮ ንግግሮቹ ያልተነገረለት ነዉና ያልተዘመረለትና ያልተነገረለት ተብሎ እረኛዉ ቢዘከር እንዴት በተገባዉ ነበር እያልሁ ለመገናኛ ብዙሀን ባለሙያዎች ስለእረኛዉ ትዘምሩለት ዘንድ በእጩነት አቅርቤላችኋለሁ፡፡

23/06/2008 ዓ.ም ደ/ወርቅ




[1]እመም ማለት በአርሶ አደሩ ማህበረሰብ ዘንድ ሰብሉን ለማረም ወይም ለማጨድ የተሰበሰቡ ሰዎች ከመሬቱ አንድ ጫፍ ወደ ሌላኛዉ ጫፍ በአንዴ የሚወጡት ወይም ይዘዉት የሚሄዱት መስመር ነዉ፡፡ እመሙ ሰፊ ወይም ጠባብ ሊሆን ይችላል፡፡ የሚወሰነዉ በአራሚዎች አልያም በአጫጆች ቁጥር ነዉ፡፡

Wednesday, October 24, 2018

እዉነተኞች መምህራነ ወንጌል ዛሬ ላይ ይኖሩን?


መምህር የሚለዉ ስም ከድንጋይ ይከብዳል፡፡ በመጀመርያ ይህ ስም ወንጌል ደጋግሞ እንደሚነግረን የጌታችን የመድሀኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መጠርያ ነዉ፡፡ ስለዚህ ማንኛዉም ፍጡራን ሊሸከሙት አይቻላቸዉም፡፡ ሲቀጥል ራሳቸዉን ክደዉ መስቀሉን ተሸክመዉ መድሀኔአለምን የተከተሉት የሀዋርያት መጠርያ ነዉ፡፡ በሁዋላም መናፍቃንን ድል የነሱ አንገታቸዉን ለሰይፍ የሰጡ መንበራቸዉን ትተዉ የተሰደዱት የሊቃዉንት መጠርያ ነዉ መምህር የሚለዉ ከባዱ ስም፡፡ መሬት ሲያረጅ ጃርት ያፈራል እንዲሉ ቤተክርስትያን ባታረጅም ዛሬ ዛሬ በዙርያዋ ጃርቶች መፈልፈላቸዉ አልቀረም፡፡ እናም ጃርቶች መምህራን እየተባሉ መጠራት ጀመሩ፡፡ በዚህ ዘመን በቤተክርስትያናችን አንድ ሰዉ መምህር ነኝ ብሎ በእነዮሀንስ አፈወርቅ፣ቄርሎስ፣ አትናቴዎስ፣ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ በቆሙበት አዉደ ምህረት ቆሞ ለማስተማር በጉባኤያቸዉም ተቀምጦ ለማስቀጸል ቢያንስ ሁለት ነገሮችን ያሟላ መሆን ይገባዋል፡፡
1. በመምህርነት ሙያ ያስመሰከረ
2. ባይማርም በእግዚአብሄር የተመረጠ

እግዚአብሄር በማይመረመር ጥበቡ ከታናናሾች መካከል ከሚመርጠዉ መምህር ዉጭ (ይህም በደጋጎች ዘመን ነበር) በኢትዮጵያ ቤተክርስትያን መምህር ለመሆን መንገዱ አንድ ብቻ ነዉ፡፡ እርሱም ቤተክርስትያናችን ካሉዋት አራቱ ጉባኤያት ማለትም አቋቋም፣ ቅኔ፣ ዜማነና መጽሀፍ ቤት በመጨረሻዉ እርሱም በመጽሀፍ ቤት ጉባኤ ገብቶ ጠንቅቆ ተምሮ ምስጢር አደላድሎ ያስመሰከረ መሆን አለበት፡፡ ይህ ለአዉደምህረት አገልግሎት ብቻ ነዉ፡፡ በቤተክርስትያናችንም መምህር የሚባሉ ሰዎች ከሚከተሉት ሙያዎች በአንዱ፣ በሁለቱ አልያም በሁሉም ያስመሰከሩ መሆንም አለባቸዉ፡፡

የቅኔ መምህር፣የአቋቋም መምህር፣የዜማ መምህር፣የመጽሀፍ መምህር፡፡ በእነዚህ ሙያዎች ሳያስመሰክር መምህር ተብሎ በአዉደ ምህረት የሚቆም ሰዉ ትንቢቱ የተነገረበት ሰዉ ይመስላል፡፡ አንድ በቤተክርስትያን መምህር ተብሎ የሚጠራ ሰዉ ከእዉቀቱ በተጨማሪ ክህነት ሊኖረዉ ይገባል፡፡ በወንጌል በጎቼን ጠብቅ፣እንዲሁም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችሁ ደቀመዛሙርቴ አድርጓቸዉ የተባሉት ካህናት ናቸዉና፡፡

ወደ ቀደመዉ ነገር እንመለስና አንድ በቤተክርስትያናችን መምህር የሚሆን ሰዉ ወደ መጽሀፍ ቤት ጉባኤ ከመሄዱ በፊት የሚጠበቁበት ሁለት አበይት ቁም ነገሮች አሉ፡፡ ስለ እነዚህ ቁም ነገሮችና አጠቃላይ ስለ መጽሀፍ ቤት ጉባኤ ምንነት ሳነብ ካገኘዉት መረጃዎችን ከቤተክርስትያን ሰብስቦ ጥናት የተደረገበትን የአንድ ታላቅ መጽሀፍ ዳሰሳን እንደሚከተለዉ አስፍሬዋለሁ፡፡

Two of the requirements for going to Metshaf bet are knowledge of qene and proficiency in Ge’ez. Metshaf bet has four Gubae;
1. New Testament takes 4-5 years to complete with its 35 books.
2. Old Testament takes 6-7 years to complete its 46 books
3. Book of Liqawuint takes 6-8 years
4. Books of Monks the study of the life of monks takes 3-4 years
It would take a student 19-21 years to complete Metsehafe bet. This did not include the time the student spent at Nibab Zema and Qene bet.

ከላይ እንደሚነበበዉ መምህር ተብሎ የሚሾም ሰዉ መምህር ከሚያስብለዉ መጽሀፍ ቤት ጉባኤ ከመዝለቁ በፊት ሁለቱ የሚያሟላቸዉ ቁም ነገሮች
1. ቅኔን መጠንቀቅ
2. ግእዝንም ጠንቅቆ ማወቅ ነዉ፡፡

ሙሉ ቅኔን ተምሮ ለመጨረስ ከትንሹ ባለ 2ት ስንኝ ጉባኤ ቃናን እስከ ትልቁ ባለ 12 ስንኝ እጣነ ሞገር ጠንቅቆ መማር ይጠይቀል፡፡ ባጠቃላይ ቅኔን ለመጨረስ እስከ 7 አመት እንደሚፈጅ ሀይማኖታዊ ድርሳናት ያትታሉ፡፡ ከላይ እንደተገለጸዉ በመጽሀፍ ቤት አራት ጉባኤያት አሉ፡፡ አንድ መምሀር ቢችል ሙሉዉን መማር አለበት፡፡ እርሱም አራት አይና ተብሎ ለቤተክርስትያን በሁሉም የሙያ መስክ የሚጠመድ በሬ ይሆናል፡፡ ካልሆነም ቢያንስ አንዱን ጉባኤ መጠንቀቅ አለበት፡፡ አንድ በአንድ እንይ፡፡

መጽሀፈ አዲሳት፡ የሀዲሳት መምህር ለመሆን ከ4-5 አመት መማር አለበት፡፡ በዚህም ቆይታዉ 35 መጽሀፍትን ተምሮ ይጠነቅቅና ለሀዲሳቱ አንገቱን አስከመስጠት ተጠያቂና ምስክር ይሆናል፡፡ ይህን ጠንቅቆ አስመስካሪዉ መምህሩ መምህር ብሎ ሲሾመዉ ያስመሰከረበትን ሙያ የሚገልጽ ማእረግ አብሮ ይሰጠዋል፡፡ መጋቢ ሀዲስ የሚል፡፡ መምህሩ ግን ያፈራዉን እዉቀት በህይወት/በተግባር መኖሩን ገና ሳያዉቅ በዚህ ማእረግ ቢገባዉም እንኩዋን ሊጠራበት አይወድም፡፡

መጽሀፈ ብሉያት፡ አንድ ሰዉ የብሉያት መምህር ለመሆን ከ6-7 አመት በጉባኤ መማር አለበት፡፡ በዚህም ቆይታዉ 46 መጽሀፍትን ተምሮ ሚስጥራትን ጠንቅቆ ይወጣል፡፡ እንደሀዲሳቱ ሁሉ ለብሉዩም መምህር የሙያ ማእረግ መጋቢ ብሉያት ተብሎ ያስመሰክራል

መጽሀፈ ሊቃዉንት፡ ስለእቅበተ ሀይማኖት፣ ዶግማ መምህር ለመሆን ከ6-8 አመት ይማራል፡፡ በዚህም ሀይማኖተ አበዉን፣ የእነቅዱስ ቄርሎስ፣ አትናትዮስ፣ ባስልዮስ ጎርጎርዮስ ዮሀንስ አፈወርቅ፣ ኤፍሬምና ሌሎች ታላቅ አባቶችን ድርሳን ይጠነቅቃል፡፡ በተጨማሪም ፍትሀ ነገስቱን ባህረ ሀሳቡን ፌሳሎጎስን (ስለ እንስሳትና እጽዋት የሚያጠና) ያስሄዳል፡፡ ሲጠነቅቅም ሊቀሊቃዉንት በሚል የማእረግ ስም ያስመሰክራል፡፡

መጽሀፈ መነኮሳት፡ አንድ የመጽሀፈ መነኮሳት መምህር የሚሆን ሰዉ ከ3-4 አመት በጉባኤ መማር አለበት በዚህም ቆይታዉ ሶስቱን መጽህፈ መነኮሳት ይጠነቅቃል፡፡
በአጠቃላይ ከእግዚአብሄር በታች ለቤተክርስትያን ዋልታ እና መከታ የሚሆን አንድ ሰዉ በመጀመርያ ለጌታችን ቀጥሎ ለሀዋርያቱ የተሰጠዉን ሊሸከሙት የማይቻለዉን ከባዱን ስም ‘’መምህር’’ን ለመሸከም ከ19-21 ዓመት መማር አለበት፡፡ ይህም አስቀድሞ ቅኔን ለመማር የሚፈጀዉን 7 አመት ሳንጨምር ነዉ፡፡

የዛሬ መምህሮቻችን በእዉኑ መምህራነ ወንጌል ናቸዉን?
ይህን የምንመዝነዉ በእኛ አእምሮ ያይደለ በመጽሀፍት መለኪያነት ነዉ፡፡ መጽሀፍት በቤተክርስትያናችን አንድ ሰዉ መምህር እንዴት እንደሚሆንም ሲማር የት በማን ሲማር እንደሆነ ጠንቅቀዉ ያስረዳሉ፡፡ በእነዚህ ሚዛንነት የዛሬ መምህሮቻችንን ብንለካቸዉ ምን ይመስሉ ይሆን፡፡

ዛሬ ላይ ቴዎሎጂ የሚባል ዘመናዊ ት/ትቤት ተከፍቱዋል፡፡ በእዉነቱ እነዚህ ት/ትቤቶች ኢትዮጲያዊ ትዉፊትን የጠበቁ እዉነተኛ መምህሮቻችንን ያስገኝልናልን? በመጽሀፉ መሰረት በመጽሀፍ ጉባኤ ቤት የተማሩት መምህሮቻችን ጥሬ አልያም ኮቸሮ እየቆረጠሙ ከአለም ተለይተዉ በጾምና በጸሎት ተጠምደዉ ነዉ፡፡ በቲዎሎጂ ዘመናዊ ት/ትቤት የተማሩት ደግሞ በኤክስቴንሽን ነዉ የተማሩት፡፡ እርሱም በአለም ስራቸዉ ሀጥያትም ይሁን ጽድቅ ሲወጡ ሲወርዱ ቆይተዉ በትርፍ ጊዜያቸዉ የሚማሩት ነዉ፡፡ መለኮታዊዉን የእግዚአብሄር ቃል ተምሮ መምህር ሆኖ ለማስተማር ተበልቶ ተጠጥቶ ሆድ ሲሞላ ደረት ሲቀላ የሚያስተምር ቴዎሎጂ እዉነተኛ መምህራንን ያፈራ ይሆን፡፡ መምህሮቻቸዉም በነጻ የሰጠዋችሁን በነጻ ስጡ የሚለዉን ቃል ንቀዉ በገንዘብ በደሞዝ አይደለምን የሚያስተምሩት፡፡ ተማሪዉም የእግዚአብሄርን ቃል በገንዘብ ይገዛል፡፡ ሲመረቁም ገንዘባቸዉን ለማስመለስ ይመስላል መጽሀፍ ጻፍን ብለዉ፣ ካሴት አሳተምን በማለት ቀጥታ ወደ ንግዱ ይገባሉ፡፡ ለዛዉም የእግዚአብሄርን ቃል፡፡ በኒህ ተማሪዎች አልፈርድባቸዉም፡፡ መምህሮቻቸዉ ያሳዩዋቸዉን ነዉና የተከተሉት፡፡ ቀድሞ መልካም መምህር መምረጥ ግዴታቸዉ ነበረርና ከመጠየቅ ግን አይድኑም፡፡

ሁሉም ይሁን ሆኗልም ቤተክርስትያንን የሚያሳፍራት ግን መምህር ተብለዉ ሲጠሩ፣ ተጠርተዉም በአዉደምህረት ሲቆሙ እነሱም ይገባናል ብለዉ ሲቀበሉት ነዉ፡፡ እንደእዉነተኞች መምህራኖቻችን ቅኔን ጠንቅቀዉ ይሆን፣ ግእዙ ገብቱዋቸዉ ይሆን፣ እሽ የየትኛዉስ መጸሀፍ መምህር ናቸዉ፡፡ የሀዲስ፣የብሉይ፣የሊቃዉንት፣የመነኮሳት፣የአቋቋም፣የቅኔ፣የዜማ፣በእነዚህ ጉባኤያት ስንት አመት ተማሩ፡፡ መልሱ አልቦ ነዉ፡፡ የአንዱም ስላልሆኑ ሲያስተምሩ ካስተዋላችሁ ርእሱ ከአንዱ መጽሀፍ ተመርጦ ሳለ የማይነካኩት ጥቅስ፣የማይዳስሱት መጽሀፍ የለም፡፡ ትምህርታቸዉም እንደአለማዉያን ሁሉ እዉቀታቸዉን እንጅ ህይወታቸዉን አይደለም የሚገልጸዉ፡፡ እዉቀት የተማረ ምእመን ደግሞ ምን እንደሚመስል አቡነ ሽኖዳ እንዲህ ብለዉናል፡፡ የሚያስተምርህ መምህር እዉቀቱን ከሆነ ሊቅ ትሆናለህ ህይወቱን ከሆነ ደግሞ ክርስትያን ትሆናለህ ይላል፡፡ ለነገሩ የዛሬ ዘመንም ምእመን እዉቀት ስለሆነ የሚሻ ሰይጣን አመቻችቶለታል፡፡ ለምእመኑስ እንደ አርዮስ ሊቅ ሆኖ ሲኦል ከመወርድ እንደ አላዛር ድሀ ሆኖ በአብርሀም እቅፍ መኖር ለዉድድር ሚቀርብ ሀሳብ ይሆንን
የዛሬ መምህሮቻችን የትኛዉን መጻፍ እንዳስመሰከሩና የየትኛዉ መምህር እንደሆኑ ቢለዩልን ምናለ፡፡ ስንት አመት ተምረዉ ነዉ ከየትኛዉ ጉባኤና መምህርስ አስመስክረዉ ነዉ ግሱን፣እርባታቸዉን፣ሰዋሰዉን ጠንቅቀዉ ሳይሆን መጋቢ ሀዲስ፣መጋቢ ብሉይ ወዘተረፈ የሚባሉት፡፡

በኋለኛዉ ዘመን ሀሰተኞች መምህራኖች ይነሳሉ ያለን ትንቢት እነዚህ መምህሮቻችን ሳይሆን ይቀራልን፡፡ እዉነተኛ መምህራን ላለመሆናቸዉ ግብራቸዉ ይናገርባቸዋል እኮ፡፡እንዴት
• እዉነተኛ መምህር የጌታን ወንጌል ላልተዳረሱት ለአረማዉያን አስተምሮ የስላሴን ልጅነት ያሰጣል ካልተቀበሉት ተወግሮ ሰማእትነተን ይቀበላል፡፡ እኛ ግን ካሉን ብዙ መምህር ተብየወቻችን አንዱንም አርያ ሆኖን አላየንም፡፡ የዛሬ መምህር ተብየዎቻችን አዉደ ምህረት ወጥቶ የሌሎችን እምነት ከመንቀፍ በቀር አንድም መምህር በራሱ ተመርቶ እንደ ሀዋርያት እና ሊቃዉንት አባቶቻችን በሚነቅፋቸዉ ሰዎች ጉባኤ ተገኝቶ እስላሙን ያስተማረ ጴንጤዉን እየሰበከ ብሎም የመለሰ የለም፡፡ በእኛዉ በዘመናችን እንኳ እነአያሌዉ ታምሩ አህዛብን እዉነት ካመኑበት ለምን አንነጋገርም እያሉ እዉነተኛ መምህርነታቸዉን ባስመሰከሩበት አዉደ ምህረት ዛሬ ቡችሎች ይፈነጩበታል፡፡
• እኒህ መምህሮቻችን ጩኸታቸዉ ሁሉ አዉደምህረት ላይ ነዉ፡፡ እዚህ ቦታ ላይ ደግሞ የጸኑ ክርስትያኖች ናቸዉ ያሉት፡፡ ጩኸታቸዉም ፍሬ አልባ ከመሆኑ የተነሳ አንዳቸም ሊያድን አልቻለም ጭራሽ ምእመናኑን ከማደንዘዝ ዉጭ፡፡ እስኪ ማን ነዉ በእነሱ ተምሮ አለምን ንቆ የመነነዉ፣ ማንነዉ የመነኮሰዉ፣ በእነሱ የተማረ ሰዉ ሀሜተኛ፣ዉሸታም፣አደለም ጠላቱን ወንድሙን የሚጠላ በመቃሙና በማጨሱ የቀጠለ አይደለም የሆኑት፡፡
• ለእናንተስ ምንም አይኑራችሁ የተባሉት መምህራን ወንጌልን በብር (በዉሎ አበል) ያስተምራሉ፡፡ ለማደርያቸዉ የተመቼ ሆቴል ለምግባቸዉ የላመ የጣመ ይጠይቃሉ፡፡ በእዉኑ መምህራኖቻን ከምእመናኑ ይለያሉን፡፡ እንዴት የጳዉሎስና የጴጥሮስ በረከት ሊያድርባቸዉ ይችላል፡፡

ጌታስ እናንተ ግን መምህር ተብላችሁ አትጠሩ፤ መምህራችሁ አንድ ስለሆነ እናንተም ሁላችሁ ወንድማማች ናችሁ ማቴ 23፡8፡፡ የዛሬ ሰባክያን አቤት መምህር ተብለዉ ሲጠሩ የሚሰማቸዉ ፍስሃ አቤት ደስታቸዉ፡፡

5/5/2009

Friday, October 19, 2018

ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል

አባባል ትልቅ ሀብት ነዉ፡፡ ሰዉን በአጭር መንገድ ቶሎ ያግባባል፡፡ አብዛኛዎች አባባሎች ሲወርዱ ሲዋረዱ የመጡ ናቸዉና ትዉፊታቸዉን ጠብቀዉ ሊሄዱ መልእክታቸዉ ሳይዛባ ሊነገሩና ሊጠበቁ ይገባል፡፡ አንዳንዴ ግን አንዳንድ አባባሎችን ትክክለኛዉን መልእክታቸዉን ገልብጠን ስንረዳቸዉና ስንጠቀምባቸዉ ይስተዋላል፡፡ ከእነዚህ ትክክለኛ  መልእክታቸዉ ተገልብጦ ከሚነገሩ አባባሎች መካከል አንዱ ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀድዶ ይሰፋል ነዉ፡፡ ይህ አባባል የምንኩስና ህይወትን በተመለከተ የሚነገር ነዉ፡፡ምንኩስና የሰዉን ልጅ ከሰማያዉያን መላእክት ጋር አንድ የሚያደርግ በፈቃድ የሚቀበሉት ታለቅ ተጋድሎ ያለበት ክብር ነዉ፡፡ ከመላእክት ጋር የሚያመሳስለዉም አንድ በምንኩስና ህይወት ዉስጥ ያለ ሰዉ የዘወትር ስራዉ እስከ ጊዜ ጥሪዉ ድርስ እንደመላእክቱ 24 ሰዓት በጾም በጸሎትና በምስጋና ፈጣሪዉን ማገልገል ብቻ ስለሆነ ነዉ፡፡ፕሮፌሰር ጌታቸዉ ሀይሌ በደቂቀ እስጢፋኖስ መጽሀፋቸዉ ገጽ 64 የህዳግ ማስታወሻቸዉ ላይ ስለ ምንኩስና ያሰፈሩትን እንይ፡፡

አንድ ሊመነኩስ የፈቀደ ሰዉ መጀመርያ በፈቃዱ ከአለም መለየቱን ከዚያም የምንኩስና ኑሮዉ ምን እንደሚመስል የሚያስረዳ ጽሁፍ ያነቡለታል፡፡ በእግዚአብሄርና በሰዉ ፊት ድምጹን ከፍ አድርጎ ሲስማማ ከፊታቸዉ ያጋድሙትና የጠጉር ልጪት፣ ቀጥሎ ለምንኩስናዉ በሚሆን ልብሱ በሰዉየዉም ላይ እንደሞተ ሰዉ ጸሎተ ፍትሀት ይጸልያሉ፡፡ ከዚያ በሁኋላ መጀመርያ መምህሩ (የገዳሙ አበምኔት) ቀጥሎ በፍትሀቱ የተካፈለዉ ሁሉ ይባርከዉና ያለብሱታል፡፡ የመጨረሻዉ ጸሎት ተጸልዮለት የምንኩስናዉን ህይወት ይጀምራል፡፡ እንደህጉ ቢሆን ከጥቂት አመታት በኋላ ደግሞ አስኬማ የሚባል ልዩ ልብስ ይሰጠዉና ወደ ከፍተኛዉ ደረጃ ይሻገራል፡፡ አስኬማ ከነት የሚሰራ 12 የመስቀል ምልክት ያለበት ቆዳ ነዉ፡፡ እንደ ህጉ ቢሆን ከአስኬማ በኋላ መነኩሴ ከገዳም አይወጣም፡፡ የመጀመርያዉን አስኬማ ለመጀመርያዉ መነኩሴ ለአባ እንጦንስ የሰጠዉ መልአኩ ስለሆነ ልብሱ አስኬማ መላአክት (የመላክት ልብስ) ይባላል፡፡ መነኮሳቱም የምድር ላይ መላአክት ይባላሉ፡፡ አሁን ግን የመነኮሳቱን ልብስ አስኬማ ይሉታል፡፡

ምንኩስና የክብሩን ያህል ጋሩም እጅግ ብዙ ነዉ፡፡ አሁን ማተኮር የሚያሻዉ ጋሩ ወይም መከራዉ ላይ ነዉ፡፡ ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል የሚለዉ አባባል የምንኩስናጋሩን የሚያሳይ ትክክለኛ ኢትዮጵያዊ ቢሂል ስለሆነ ጋሩን ስንተነትን ብሂሉ ምን እንደሆነ በደንብ ይገባናል፡፡አንዳንድ ሰዎች ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል ሲባል መነኩሴ ስራ ስለሌለዉ ዝም ብሎ ቁጭ ከሚል ቆቡን ቀዶ መስፋት የሚወድ የሚመስላቸዉ አሉ፡፡ አባባሉ የሚነገረዉ ግን በተቃራኒዉ ስራ ለበዛበት እና ባተሌ ለሆነ መነኩሴ ነዉ፡፡ እንዴት እንደሆነ በዝርዝር እንይ፡፡ አንድ መነኩሴ በማህበር በገዳም ወይም በተባትሆ በበርሀ ሲኖር ህይወቱ በሙሉ ለ24 ሰዓት ምስጋና የተሰጠች ናት፡፡ ይህም የምስጋና ህይወት መነኮሱ በግሉ ከአመት እስከ አመት የሚደረሱ የ7 ሰዓት የእየለቱ ጸሎቶችን ይይዛል፡፡ ህይወቱ ዘወትር በዚህ የተጠመደቸ ናት፡፡ በማህበርም ከአመት እስከ አመት የማይታጎለዉ ቅዳሴዉ፣ ኪዳኑ፣ ማህሌቱ፣ ሰአታቱ ሌላኛዉ የምስጋና ህይወት ነዉ፡፡ ከምስጋና ህይወት በተጨማሪ የአንድ መነኮስ ህይወት እድሜ ዘመኑን በስራ የተጠመደች ናት፡፡ በገዳም ያለ መነኩሴ ቅዱሳት መጽሀፍትን ዘወትር ማንበብ ይጠበቅበታል፡፡ መጽሀፈ መነኮሳትን፣ መጽሀፍ ቅዱስን፣ ገድላትን ተአምራትን ያነባል ይተረጉማል፡፡ በእኛ ሀገር በተለይ የመነኮሳት ስራ እጅግ የበረታ እንደነበር የቅዱሳን አባቶቻችንን ገድል ማየት እንችላለን፡፡ በመካከለኛዉ ዘመን የነበሩ መነኮሳት ከአንድ ጉባኤ ትምህርት ሲጨርሱ እንደዛሬዉ በቃል ብቻ ማስመስከር አይጠበቅባቸዉም፡፡ ይልቁንም በቃል ያስመሰከሩትን ትምህርት ብራና ፍቀዉ፣ ሌጦ አዘጋጅተዉ ይደጉሱና ብእር ቀርጸዉ የብራና ጽሁፍ ያዘጋጃሉ፡፡ ለዚህ ነበር የመነኮሳት መፍለቅያ የነበረዉ የአባ ኢየሱስ ሞአ ገዳም የኢትዮጵያ የስነ መለኮት ዩንቨርስቲ የሚባለዉ፡፡ እኒህ መነኮሳት ከዚህ በኋላ ለሌላ ትልቅ ተጋድሎ ራሳቸዉን ያዘጋጃሉ፡፡ እግዚአብሄር በፈቀደላቸዉ ገዳም ሲኖሩ የዘወትር መንፈሳዊ ስራዎቻቸዉን ከፈጸሙ በኋላ ፍጹም ተዋርዶና ትህትና ድካምንም ለሚጠይቅ የጉልበት አገልግሎት ይሯሯጣሉ፡፡

እንበለ ስጋ ኢትቀዉም ነፍስ ነዉና መጽሀፉ የሚለዉ መነኮሳት ለስጋቸዉ መጠገኛ ለሚመገቡዋት ትንሽ /ኩርማን ዳቤ ብዙ ይደክማሉ፡፡ ለዚህም አንድ የገዳም ረድ የሆነ መነኩሴ ዳቤ የሚጋገረዉን እህል በእጅ ወፍጮ ይፈጫል፡፡ ወፍጮ የሚፈጨዉ ተጎንብሶ ስለሆነ በስግደት የደከመን ወገብና የእጅ መገጣጠምያ እጅግ ይፈትናል፡፡ የፈጨዉን ዱቄት ያቦካል ይጋግራል፡፡ ከወንዝም ወርዶ ዉሃ በማሰሮ ቀድቶ በትክሻዉ ተሸክሞ ያመላልሳል፡፡ ይህ መነኮስ ዳቤዉን ከመጋገሩ በፊት ማገዶ ያስፈልገዋልና ወደ በርሃ በመዉረድ እንጨት ቆርጦ ፈልጦ ተሸክሞ ለገዳሙ ማምጣት አለበት፡፡ የፈለጠዉን እንጨት ማገዶ በጢሱም በእሳቱም እየተገረፈ መነኮሳትን አብስሎ ይመግባል፡፡ ከዚያም ለመቅደሱ ዉስጥ አገልግሎት የሚሆ ነገሮችን በማዘጋጀት ጣሩና ጋሩ ይቀጥላል፡፡ ግብር ያደቃል፣ ህብስቱን ይጋግራል፣ ወይኑን ይጠምቃል፣ ፍህም ያያይዛል፡፡ ከዚህ ድካም ሁሉ በኋላ ወደ ህያዉና እዉነተኛዉ ሰማያዊዉ አገልግሎት ይመለሳል፡፡ በትህትናና በለቅሶ በአንቃዶ ህሊና ቅድመ እግዚአብሄር ቁሞ እግሩን ሳያጥፍ ይቀድሳል፣ ያወድሳል፣ ይጸልያል፡፡ ከጸሎት ቀጥሎ ወዙ እስኪንጠፈጠፈ ጣቶቹና ጉልበቶቹ እዥ እስኪወርዳቸዉ ድረስ ይሰግዳል፡፡ ለድካመ ስጋዉ አረፍ ባለበትም ቅዱሳት መጽሀፍትን ያነባል፡፡

ይህ ምድራዊ መልአክ መነኩሴ አደለም የእረፍት ሰዓት ማግኘት ቀርቶ ስለረፍት እንኳን የሚያስብበት ጊዜ የለዉም፡፡ ሆኖም ግን ስራዉን በጊዜ ጨርሶ ምንም የሚሰራ ስራ ጠፍቶ መነኩሴዉ እንደሚቦዝን ቀድሞ ካወቀ ከላይ ያልነዉ የኢትዮጵያዉያንን አባባል ስራ ላይ ያዉላል፡፡ መነኩሴዉ ቆቡን ቀዶ መስፋት ይጀምራል፡፡ ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል ማለት ቆብን ቀዶ መስፋት ለመነኩሴ ስራ ሆኖ ሳይሆን እራስን ከዝርዉነት ለመጠበቅ የሚያደርገዉ ሌላኛዉ የመንፈሳዊ ተጋድሎ ክፍል ነዉ፡፡ ይህ ደግሞ ሰዉ ሰራሽ ህግ ሳይሆን ከፈጣሪ የተሰጠ ራስን ከፈተና የመታደጊያ መንገድ ነዉ፡፡ በግብጽ በርሃ ይኖር የነበረዉ የመጀመርያዉ ባህታዊ አባ ጳዉሊ ከፈጣሪዉ ይህ ስራ ተሰጥቶታል፡፡ አባ ጳዉሊ በብህትዉና ሲኖር ሌትም ቀንም አምላኩን እያመሰገነ በትግሀ ጸሎት ነበር፡፡ አባ ጳዉሊ ጸሎት አድርሶ ሲጨርስና አእምሮዉ ሲያርፍ ሰይጣን የአለምን ሀሳብ እያመጣ ጥሎት የመጣዉን ከንቱ ህይወት እያሳሰበ እንዳይፈትነዉ እግዚአብሄር መለአኩን ይልክለታል፡፡ መለአኩም ይመጣና ከበርሀ የበቀሉትን የዘንባባ ቅጠል እየፈተለ ምንጣፍ እየሰራ ያሳየዋል፡፡ ከዚህ በኋላ አባ ጳዉሊ ከጸሎት በኋላ ስራ ሳይፈታ ሁሌም የዘንባባ ቅጠል በመጠቅለል ምንጣፍ ይሰራ ነበር፡፡ ልብሱም በእለተ እረፍቱ አካባቢ ከቅዱስ እንጦስ ጋር ተገናኝቶ የኮፕት መነኮሳት ልብስ የሆነዉንና አባ ጳዉሊም የኮፕት ቤ/ክ ስርአት ተገዥ መሆኑን ለማስመስከር  ምልክት ይሆነዉ ዘነድ የምንኩስናን ልብስ ከእንጦንስ እስኪቀበል ድረስ ከቅጠል የተሰራ ቀሚስ ነበር፡፡

ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል የሚለዉ ብሂል ለስራ አጥ መነኩሴ ወይም መነኩሴ ስራ የለዉም ለማለት የነተነገረ የሚመስለን ሰዎች ካለን አሁን በእኛ ዘመን ከምናየዉ ሁናቴ የአንዳንድ መነኩሴ ሳይሆኑ ግን መስለዉ ከሚኖሩ ሰዎች እየተነሳን ይመስለኛል፡፡ ምክንያቱም  ዛሬ ላይ እንኳን ቆቡን ቀዶ የሚሰፋ ትጉህ መነኩሴ የተሰፋ ቆብ በትክክል የሚያደርግ መነኩሴ የለም፡፡ በትክክል የሚያደርግ ስል ሳያዛንፍ ማለቴ እንዳልሆነና የምንኩስና ቆብ ትርጉሙን በትክክል የተረዳ፣ ከነማን እንደተጫነለትና ለምን እንደተጫነለት ማለቴ ነዉ፡፡ በመካከለኛዉ ዘመን የነበሩ ኢትዮጵያዉያን መነኮሳት እኮ ሲመነኩሱ ብዙ ዉጣ ዉረድ የሚያስጉዝ መንገድ ካለበት ገዳም የሚኖር አባት አፈላልገዉ ሄደዉ ይቀበላሉ፡፡ ለዛዉም ይገባኛል ብለዉ ሳይሆን በአባቶች ተገፋፍተዉ አልያ አምላካቸዉ በራእይ ነግሯቸዉ ነዉ፡፡ አስኬማዉን እና ቅንዋቱን  ደግሞ ከሌላ ተጋድሎ በኋላ እንዲሁ አምላክ ከፈቀደላቸዉ አባት በትህትናና ራስን በማዋረድ እጅ ነስተዉ ይቀበላሉ፡፡ ዛሬ ምንኩስናን አንድ ሰዉ እንዴት ይሆን የሚቀበለዉ? በመካከለኛዉ ዘመን ይኖር የነበረዉ አባ እስጢፋኖስ እንዲህ እንደዛሬዉ ዘመን ምኩስናን ተቀብለዉ በህጉና በስርአቱ ያልተጉዋዙትን አባቶች ነን የሚሉትን እንዲህ ገስጾዋቸዋል፡፡

እነሱስ ቢሆኑ ራሳቸዉን ለአባቶቻቸን ለቅዱሳን ሐዋርያትና ተከታዮቻቸዉ ለመነኮሳት አባቶች ለእንጦንዮስና ለመቃርዮስ ትእዛዝ ሳያስገዙ የአባትነት ስም እንዴት ወለዱ?  እዉነትን የሚፈልገዉን በከንቱ የሚቃወሙ ከሆነ እኔ ደግሞ ወይ የእግዚአብሄር ወይ የእግዚአብሄር ባሮች ሁኑ እላቸዋለሁ፡፡
ዛሬም በዘመናችን የቤተክርስትያን ዘቦች ይሆናሉ ተብለዉ አለምን ንቀናል ምድራዊ መለአክ ሆነናል ብለዉ የመነኮሱ ሰዎች በስልጣንና በነዋይ ጥም ተነድፈዉ እዉነት ፈላጊ የዋህ ምእመናንን ከመንገድ ሲያስወጡ የቤቴክርስትያንን ህግና ቀኖነዋን ሲንዱ ይገኛሉ፡፡ ታድያ ያ አባባል ለእንዲህ አይነት መነኩሴዎች የተነገረ አይደለም፡፡ እንዲህ አይነት ስራ ፈት መነኮሳት በበዙበት ዘመን እማ ብሂሉ ሊሆን የሚችለዉ፡፡
ቆቡን ቀዶ የሚሰፋ፣
መነኩሴ  እኮ ዛሬ ጠፋ፡፡











Wednesday, December 6, 2017

የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ

በህብረተሰቡ ዘንድ በእለት ተእለት ኑሯችን በንግግሮቻችንም በጽሁፎቻችንም የምንጠቀማቸዉ ብዙ ሀገር በቀል አባባሎች አሉን፡፡ እኒህ አባባሎች ሰፊዉን ጠበብ፣ ከባዱን ቀለል፣ ደረቁን ረጠብ አድርገዉ መልእክትን በማቀላጠፍ እኛንም በማግባባት በኩል ትልቅ አስተዋጽኦ አላቸዉ፡፡ የእኒህ አባባሎች ዛሬ ላይ ባለቤታቸዉ ህዝብ እና ህዝብ ብቻ ነዉ፡፡ እኔ ግን ፍለጋየ እና ቢሆንልኝ የምደሰተዉ እኒህን አባባሎች ለመጀመርያ ጊዜ ከአፉ አዉጥቶ የተናገራቸዉ ግለሰብ ማን እንደሆን ማወቅ ነዉ፡፡ መቼም ህዝብ በአንድ ቅጽበት አይናገራቸዉም፡፡ ለምሳሌ ያህል ብንመለከት ሁለት እግር አለኝ ተብሎ ሁለት ዛፍ አይወጣም ያለዉ የመጀመርያዉ ግለሰብ ማን ይሆን? እግር አልባ ሰዉ ይሆን፣ ዛፍ ቆራጭ ይሆን፣ ነጋዴ፣ ገበሬ፣ ሙህር፣ ቄስ፣ ሴት፣ ወንድ፣ ወጣት፣ ሽማግሌ ከየትኛዉ ወገን ይሆን፡፡ እነ በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ፣ እነ ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል፣ እነ አህያዉን ቢፈሩ ዳዉላዉን፣ እነ አሳ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል፣ እነ አንድ ሞኝ የተከለዉን ሰላሳ ሊቃዉንት አይነቅለዉም አረ ስንቱ፡፡ ማን ይሆን አስቀድሞ በሆዱ አጭቶ ከአፉ ያወጣቸዉ፡፡
እኒህ ሰዎች ሊደነቁ ሊወደሱ ይገባቸዋል፡፡ ምክንያቱም እነሱ የተናገሩት የመላዉ ህዝብ ሀብት ሆነ፣ እኛም በንግግሮቻችን ጣልቃ እያስገባን የተንዛዛ ሀሳብ አሳጥረናል፣ ሊቅነታችንን አስመስክረንበታል ወ ዘ ተ፡፡ ከምንም በላይ ደግሞ ራሳችን የፈጠርናቸዉ መስሎናል፡፡ አንድ አስገኝ ግለሰብ እንዳላቸዉ አስበንም አናዉቅም፡፡ እርግጥ ነዉ በማህበረሰቡ የሚነገሩ አንዳንድ አባባሎች ለመጀመርያ ጊዜ የተናገራቸዉን ግለሰብ የሚጠቁሙ ጥቂቶች አሉ፡፡ ለምሳሌ ያህል በአንድ ህብረተሰብ ዘንድ የሚነገሩትን ባነሳ ጣጣ ነዉ አለ ቆምጨ አምባዉ፣ ምን ታደርጊዋለሽ አለ ጥላዉን ገሰሰ፣ ተጨንቄብሽ አለ አለሙ ብርሀኔ፣ ልግብ አለ ዳምጤ ብርሀኑ፡፡ ሁሉም አስገኛቸዉን ይናገራሉ፡፡  ይህ ማህበረሰብ የሰለጠነ ነዉ ባይ ነኝ፡፡ ለምን ቢሉ በንግግራቸዉ ወቅት ምንም እንኳ አባባሎችን ቢያስቀድሙም ተናጋሪያቸዉን ያስከትላሉና፡፡ ከፕላጃሪዝም (ከባባቤትነት ስርቆት) የጸዱ ናቸዉ፡፡ ብዙዎች አባባሎቻን ግን በሀይለኛዉ ፐላጃራይዝድ የተደረጉ ናቸዉ፡፡ ለምሳሌ ከላይ የተጠቀሱት እነ በአንድ ድንሃይ ሁለት ወፍ፣ እነ ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል፣ እነ አህያዉን ቢፈሩ ዳዉላዉን፣ እነ አሳ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል፣ እነ አንድ ሞኝ የተከለዉን ሰላሳ ሊቃዉንት አይነቅለዉም ሁሉም ምንም እንኳ አንድ አስገኝ ግለሰብ ቢኖራቸዉም ህዝቡ ሲናገራቸዉ ግን የራሱ አስመስሎ ነዉና የባለቤትነት ስርቆት ተጎጅዎች ናቸዉ፡፡
እኔም በንግግሬ ወቅት ዘመናዊ መሆን እፈልጋለሁ፡፡ የሙህራንን የመመረቅያ ጽሁፍ የሚያስተችና የሚያጎድፍ ፕላጃሪዝም የተባለ ወንጀል ሁል ጊዜ በምላሴ ስፈጽም እየሰቀጠጠኝ ነዉና፡፡ ይህ የአባባሎቻችንን ባለቤት ማወቅ ጉጉቴ የመነጨዉ በዋናነት ካለእነሱ ንግግር ስለማይሆንልኝ ከፕላጃሪዝም ለመንጻት ነዉ፡፡ የምመኘዉም እድሌ ሰምሮ እንደ እናቶቼና አባቶቼ እየተገረምኩ በወሬዎቼ መካከል ሆሆ ….. አሳ ጎርጓሪ ዘንዶ ያወጣል አሉ አቶ እገሌ፣ እም እቴ……. ስራ ያጣ መነኩሴ ቆቡን ቀዶ ይሰፋል አሉ እሞሀይ ማንቴስ……… እያሉ ከፕላጃሪዝም የጠራ ዘመናዊ ንግግር ማድረግ ነበረ፡፡
እናም ይህ የአባባሎቻችንን የመጀመርያ ተናጋሪ ሰዉ ማንነት በትክክል የማወቅ ፍላጎቴ እንደማይሳካ ስረዳ ለመገመት ተገደድኩ፡፡ ለአሁኑ ልገምት የተነሳሳሁበት ከአባባሎቻችን መካከል የሆነዉን “የአንድ ሳንቲም ሁልት ገጽታ” የሚለዉን ነዉ፡፡ ይህን አባባል ተናግሮ ያናገረን ሰዉ ምን አይነት ይሆን? የሚለዉን ጥያቄ በግምታዊ መላምት ከመለስኩ በሁዋላ እምልላችኋለሁ አባባሉን እንደ ድሮዉ እንደወረደ አልናገረዉም፡፡ ይልቁንም የአስገኝዉን ስም እየጠቀስኩ አለ እገሌ እያልኩ ባለቤቱን እያወጅኩ ከፕላጃሪዝም ነጻ ሆኜ አወራለሁ እንጅ፡፡ ለማንኛዉም የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ባይን ግለሰብም ይሁን ድርጅት ማንነት ፍለጋ ገባሁ፡፡
አንድ ሞኝ የተከለዉን ሰላሳ ሊቃዉንት አይነቅሉትም ሲሉ እሰማለሁ፡፡ ችግሩ ፕላጃሪዝም ነዉ እንጅ  እኔም ለራሴ አልፎ አልፎ ተጠቅሜዋለሁ፡፡ እዉነቱ ይሄ ሁኖ እንጅ  የአንድን ነገር ፍጹም አንድነትና አይነጣጠሌነት ለመግለጽ ብሎም ለማስረዳት የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ብሎ ለመጀመርያ ጊዜ የተናገረ ሰዉ ከሞላ ቁሳቁስ ሳንቲምን ብቻ ለመጠቀም የተገደደዉ መለኮታዊ ትእዛዝ አልያም ሌላ የተለየ አሳማኝ ምክንያት አግኝቶ አይመስለኝም፡፡ አሁን ባለንበት ቅጽበት ዞር ዞር ብለን ብናይ እኮ በዙርያችን የማይነጣጠሉ ግን ሁለት ገጽታ ያሉዋቸዉ ስንት ግሳንግስ ነገሮች አሉ መሰላችሁ፡፡ እስኪ ከራሳችሁ ጀምራችሁ የቤት እቃዎቻችሁን እዩ፡፡ እኔ አሁን አልጋየ ላይ ጋደም ብየ ይህን ስጽፍ ከፊት ለፊቴ ሶስት ተደራርበዉ የቆሙ የእናቴ የእንጀራ ማቅረብያ ትሪዎች ይታዩኛል፡፡ ሶስቱም ሁለት የማይነጣጠሉ ገጽታዎች አሉዋቸዉ፡፡ ፊትና ጀርባ፡፡ እንዳዉም እንደሳንቲም ሁሉ ዘዉድ የለዉም እንጅ ጎፈር አለዉ፡፡ የጃንሆይን ባንዲራ በቀጭን ዘንግ ሰክቶ በትክሻዉ ያነገተ ጎፈርያም አንበሳ ከፊት ከፊታቸዉ ላይ ተነድፎበት ይታያሉ፡፡ ዙርያዉን ነዉ ያልኩትና የማይነጣጠሉ ገጽታዎች ፍለጋ ወደ ጀርባ ዞሬ ሳይ ብፌ ላይ የቤተሰብ የፎቶ ፍሬሞች ከነፎቶዎቻቸዉ ተኮልኩለዉ ይታዩኛል፡፡ እነሱም ያዉ ናቸዉ፡፡ የምን ሩቅ መሄድ አስፈለገ የለበስኩት ብርድ ልብስ ለራሱ ጥሩ ምሳሌ አይደል እንዴ፡፡ የማይነጣጠል ሁለት ገጽታ አለዉ፡፡ እንዲህ ዘና የምልበት ቤቴ ራሱ ጣርያዉ፣ ኮርኔሱ ግድግዳዉ በሩና መስኮቱ የሚገርም ባለ 2D ናቸዉ፡፡
ሰዉ ግን ሳንቲምን ዝም ብሎ ዘሎ የተጠቀመ አይመስለኝም፡፡ እንዳዉም ለምን የሚል ጥያቄ አንስቶ ጥልቅ ጥናት የሚያስፈልገዉ ይመስለኛል፡፡ እንደኔ ግምት ግን ለዚህ ሰዉ ከሌሎች ገጽታዎች ሁሉ ልቆ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ትልቅ ዋጋ ሳይኖራቸዉ አልቀረም፡፡ ለማንኛዉም ግምታዊዉን ምላሽ ለማግኘት ይረዳን ዘንድ ሳንቲሞች በአብዛኛዉ ወደሚገኙበት ሰፈር ጎራ ማለት ግድ ይለናል፡፡ ሳንቲሞች ከሚዘወተሩባቸዉ ቦታዎች መካከል ገበያ አንዱና ዋነኛዉ ስፍራ ነዉ፡፡ ነገር ግን ገበያ ላይ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ምንም ዋጋ የላቸዉም፡፡ ለገጽታቸዉ ማንም ዋጋ አይሰጣቸዉም፡፡ ስለዚህ ገብያተኛ ይህን አባባል አልተናገረዉም ብለን መላምት መንደፍ እንችላለን፡፡ ሁለተኛዉ የሳንቲም መገኛ አድራሻዎች ደግሞ ቁማር ቤቶች ናቸዉ፡፡ ከራሴ ልምድ ተነስቼ ከገበያ ይልቅ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ትልቅ ዋጋ ያላቸዉ በቁማር ቤት ብቻና ብቻ መሆኑን ማሳየት እችላለሁ፡፡

የአንድ ሳንቲም ሁለቱ ገጽታዎች የተለያዩ ስሞች መኖራቸዉን የምናዉቀዉም አሁንም በቁማር ጊዜ ብቻ ነዉ፡፡ አንድ ቀን አንዱም ገጽ አቤት ብሎ አያዉቅም እንጅ ቁማርተኛ ሁሉ እኒህን ገጽታዎች ስማቸዉን እያቆላመጠ ሲጠራቸዉ ነዉ የሚኖረዉ፡፡ አንዱን ገጽ ጎፋ (ጎፈር) እያለ ይጠራዋል ሌላኛዉን ዘዉድ ይለዋል፡፡ ታድያ በመቆመር ጊዜ እኒህን የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ስሞች ግብሮችና ልዩ ምልክቶች ጠንቅቆ ማወቅ አዉቆም በገጽ መጥራ ተቀዳሚ መስፈርት ነዉ፡፡ ይህ እዉቀት የራስን ገንዘብ ፈቅዶ ተጫዉቶ ከመበላት አልያም ካሸነፉ የቋመጡለትን የአቻን ገንዘብ እንዳያመልጥ ሞልቅቆ ለማምጣት ቁልፎች ናቸዉና፡፡ የጨዋታዉ ሰልፍ ይህን ይመስላል፡፡ ሲቆመር ሳንቲም  የያዙ የቆማሪ መዳፎች አንዱ ባንዱ ላይ ተደራርበዉ የገበሎ አስተኔ ስብስብ መስለዉ ይቀመጣሉ፡፡ ከእያንዳንዱ መዳፍ እቅፍ ዉስጥ ላብ የሚያጠምቃት በዘዉዱ ይድፋት በጎፈሩ ባለቤቱ ብቻ የሚያዉቃት ሳንቲም ትወሸቃለች፡፡ ከዚያም በላይ ያለዉ ግለሰብ መዳፉን ያነሳና ሳንቲሙ የወደቀችበትን የላይኛዋን ገጽ በጥንቃቄ ያያል፡፡ ቀጥሎ ከስር ያለዉ ተጫዋች መዳፉን ቀስ ብሎ ያነሳና እንዲሁ የሳንቲሙን የላይኛዉን ገጽታ ያሰተዉላል፡፡ የእሱ የሳንቲም ገጽታ ከላይ ከነበረዉ የሳንቲም ገጽታ ጋር ከተመሳሰለ የላይኛዉ ገንዘቡን ይወስዳል (በእነሱ አባባል ይበላል) የታችኛዉ ተጫዋች ሳንቲም ገጽታ ከላይ ካለዉ ከተለየ የታችኛዉ ይበላል፡፡
አዎ ለመበላላትም ላለመበላላትም ቁማርተኞች የአንድን ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች የራሳቸዉን ያህል ያዉቁዋቸዋል፡፡ በቁማርተኞች ዘንድ የአንድን ሳንቲም ሁለት ገጽታ ማወቅ ከመበላት ያድናል፡፡ እኛ ከመበላት የምንድነዉ መሳርያ ታጥቀን ዋሻ ገብተን ቤት ዉስጥ ዘግተን አይደለ፡፡ ስለዚህ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ ለቁማርተኛ የመሳርያ የቤትና ዋሻ ያህል ናቸዉ ማለት ነዉ፡፡ ይህ እንግዲህ አንድ ሀቅ ያሳየናል፡፡ እሱም የአንድ ሳንቲም ሁለትጽታ ብሎ የተረተዉ፣ የተናገረዉ የመጀመርያዉ ግለሰብ የሳንቲም ገጽታዎች ህይወቱ የሆነዉ ቁማርተኛ ሰዉ መሆኑን ነዉ፡፡ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታዎች ዋጋ ያላቸዉ ለቁማርተኛ ብቻ ነዋ፡፡ ለነጋዴዉም ሆነ ለገበሬዉ ለለማኙም ሆነ ለሙህሩ ዋጋዉ ራሱ ሳንቲሙ እንጅ የሳንቲሙ ገጽታዎች አይደሉም፡፡ አስተዉላችሁ ከሆነ በንግድ ጊዜ ሰዎች ሳንቲም ሲቀያየሩ የሚመለከቱት አምስትነቱን፣ አስርነቱን፣ ስሙኒነቱን፣ ሽልንግነቱን ዛሬ ዛሬ ደግሞ አንድ ብርነቱን እንጅ እንደቁማርተኞች ዘዉዱንና ጎፈሩን ወይም ገጽታዉን አይደለም፡፡ በቁማር ጊዜ ደግሞ  ዘዉዱነት ጎፈርነት እንጅ ስሙኒ ሽልንግነት ከቁብ አይገቡም፡፡ ለዚህም አይደል እንዴ ባለዘለሰኛዉ በቁማርተኞች የሳንቲሞች ዋጋ ሳይሆን ገጽታ መለከፍ ተደንቆ የተቀኘባቸዉ እንዲህ ሲል
ቁማር ጨዋታ ተጫዉቼ፣
አጨብጭቤ ቀረዉ ተረትቼ፣
ምንኛ እድሌ በሰመረ፣
ዘዉዱን ገልብጨ በነበረ፡፡
የቁማርተኛ ጥቅስ እንዲህ ይጠቅማልና አንድነትን ለማወፈር ተመሳሳይነትን ለማጠንከር አንድ ቁማርተኛ የተከለዉን  እኛም ሰላሳና ከዚያ በላይ ሆነን ይህን ቃል ሳንነቅለዉ ስናስተጋባዉ እንኖራለን፡፡ ታድያ ከዚህ ወድያ ከባለቤትነት ስርቆት ተላቅቄ የሰለጠነ ንግግር ልናገር ለራሴ ቃል ገባሁ፡፡ የአንድ ሳንቲም ሁለት ገጽታ አለ ቁማርተኛ እያልኩ፡፡











Monday, July 3, 2017



ነገረ-ጠጅ
(የተጣለ መጠጥ)
እነሆ በሀገራችን መጠጥ ይጣላል (ጠጅ) ይሾማል (ጠጅ) ይበጠበጣል (ጠላ) ይጠመቃል (ጠላ) ይወጣል (አረቂ)፡፡ እኒህን ሀገር በቀል አባት አደር ባህላዊ መጠጦች አንድ የሚያደርጋቸዉ ባህርይ አላቸዉ፡፡ የእኛን ሙሉዉን ሳይሆን የቅርብ ጊዜ ዘመን አያድርገዉና መጠጦቹ የሚጣልባቸዉ፣ የሚሾምባቸዉ፣ የሚበጠበጥባቸዉ፣ የሚጠመቅባቸዉና የሚወጣባቸዉ እቃዎች ከሸክላ መሰራታቸዉ ነበር፡፡ በኋለኛዉ በእኛ ዘመንማ ቫይረስ ይከላከል ይመስል የላስቲክ እቃ ሁሉ ሸክላን እየገፈተረ ጥልቅ ማለት ጀመረ፡፡ እኒንያ የሸክላ እቃዎች ማሰሮ፣ እንስራ እና ጋን ናቸዉ፡፡ ጋን ከሸክላ የሚሰራ የወግ እቃ ሲሆን ምናልባትም በሀገራችን ከባህላዊ የቤት ቁሳቁሶች ትልቁ ሳይሆን አይቀርም፡፡በሃገራችን በነገስታት ዘመን አንድ ታላቅ ጋን እጅግ ማለፍያ የሆነ አገልግሎት ነበረዉ፡፡ እርሱም ለንጉሱና ሹማምንቶቹ የሚሆን ባለሙያ ሴት የጠመቀችዉ ጠጅ መሾምያነት ማገልገል ነበር፡፡ ጠጅ እጅግ የተወደደ የክብር መለክያ የሆነ መጠጥ ስለነበር በከበረ እቃ ማለትም በጋን ተሹሞ ጋኑም በክብር ቦታ ለብቻዉ በእልፍኝ ዉስጥ ይቀመጣል፡፡ ጠጁ በጋን መዘጋጀቱ ከጠጁም ከጋኑም ክብር የተነሳ ጠጁ ጋን ተሾመ እሰከመባል ድረስ የሹመት ማእረግ ነበረዉ፡፡ ይህ በጋን የተሾመዉ ጠጅ በንግስናና በምስፍና ለተሸሙት ሰዎች በማእረግ ይወርዳል ይጠጣል፡፡  

ዉሎ ዉሎ ከቤት ኑሮ ኑሮ ከሞት አይቀርምና ሹመት ይሻራል ንግስናም ይቀራል፡፡ በሀገራችን ንግስና ሲቀር ጠጅም መሾሙ ቀረ፡፡ መጠጣቱ ግን አልቀረም፡፡ ንግስና ከቀረ በኋላ ኢትዮጵያዊት እናት ጠጅ ሾምኩ ሳይሆን የምትለዉ ጠጅ ጣልኩ ነዉ፡፡ እናም አባቶች  የነገስታትን ዘር ተዋግተዉ አዳክመዉ ንጉስ በዙፋን መሾም ሲቀር እናቶች ደግሞ ጠጅ በጋን መሾሙን አቁመዉ በሮቶ መጣል ጀመሩ፡፡ እናቶች ጠጅ ጣልኩ ይበሉን እንጅ እንዴት እንደጣሉት ያወቁ አይመስለኝም፡፡ጊዜ ሰጥቷቸዉ እስከዚህ ዘመን የደረሱ የተሾመም የተጣለም ጠጅ የጠጡ አዛዉንት አባቶች እንደሚናገሩት ከሆነ እናቶች ጠጅ መጣል የጀመሩት በሶስት መንገድ ነዉ ይላሉ፡፡

  • ·         ማር ለከለር ብቻ ተጨምሮ ጠጁ በስኳር መጠመቅ ሲጀምር፡
  • ·         ጋን ከእልፍኝ ጠፍቶ ማድቤት በተቀመጠ ጎማ ሲጠመቅ፡፡
  • ·         ለንጉስ ቀርቶ ለህዝብ መዉረድ ሲጀምር ጠጅ መጣሉ ተጀመረ፡፡

ታድያ እኒህ አባቶች ስናገሩ እንደምንሰማዉ ከሆ በሀገራችን የጠጅ ሹመት ከንግስና ሸረት ጋር አብሮ ከስሞ ቀርቷል፡፡

ከላይ አብረን እንዳየነዉ የተሸመ ጠጅ ደንበኞች የማንም አልፈ ሂየጅ ሳይሆን ነገስታቱ መኳንንቱ፣ መሳፍንቱና ልኡላኑ ነበሩ፡፡ የተጣለ ጠጅ ደንበኞችሳ አትሉኝም፡፡ እነሱማ  አብዛኛዎቹ ኑሮ የጣላቸዉ የሚመስሉ ሊጠጡ ሲሄዱ ትያትር ሲተዉኑ ቆይተዉ ከመድረክ ወረዱ የሚመስሉ ናቸዉ፡፡ እንዴት ቢሆን አትሉኝም፡፡ እንዲህ ነዋ፡፡ አለባበሳቸዉንስናይ ከመሃል በእላቂ ካፖርት አልያም ረጅም ጃኬት ዉስጥ የተደበቁ ከታች ባት ከጉልበት በሚሸፍን ቦት ጫማ ገብተዉ የሚንደፋደፉ ከላይ ደግሞ አይንና አፍንጫን አፍና የምትይዝ አሮጊት ኮፍያ ያጠለቁ በእድሜ አባዋራ፣ ወጣትዋራ እና አሁን አሁን ደግሞ እማዋራ የሆኑ ናቸዉ፡፡ እኒህ ዋራዎች አካሄዳቸዉን ስናይ የተጣለዉን ጠጅ ለመጠጣት በእጃቸዉ ሰንጣራ ዘንግ ወይም ከዘራ ተመርኩዘዉ ሰአት አመራረጣቸዉ ደግሞ ጸሀይ ብቅ ወይም ዘቅዘቅ ስትል ማዝገም የሚጀምሩ ናቸዉ፡፡ የሚገርመዉ የአሁኑ ጊዜ ጠጅ መጣሉ ብቻ ሳይሆን መጣሉ (አላልተህ አንብብ) ጭምር ነዉ፡፡ እናም እኒህ የጠጅ ደንበኛ ዋራዎች እንዲህ ከእግር እስከ ራሳቸዉ መልበሳቸዉ ጠጁ እንደሚጥላቸዉ ስላወቁ ነዉ ተብለዉ ይታማሉ፡፡ እንዳይወድቁ ዘንግ ወይም ከዘራ ይመረኮዛሉ፡፡ ዘንጉ አልችላቸዉ ብሎ ከወደቁ ወድቀዉ እንዳይቀሩ ቅልጥማቸዉን በቦት ወገባቸዉን በካፖርትና አናታቸዉን በኮፍያ ከጉዳት ይከላከላሉ፡፡ በተለይ የኮብልሰቶን መንገድ ከመጣ ወዲህ እንዲህ እንዲቀጥሉ አስገድዷቸዋል፡፡ አንድ በማህበረሰባዊ ህይወት ዙሪያ ዳሰሳ እያደረገ በብሎግ ለህብረተሰቡ መረጃ ሚያጋራ ጦማሪ እንዲህ ጦምሮ ነበር፡፡ መንግስት ህዝቡ እንዲወድቅ የቢራ ፋብሪካዎችን ይከፍታል፣ ወድቆ እንዳይነሳ ደግሞ ኮብልሰቶን መንገድ ይሰራል፡፡ የጠጅ ደንበኛ ዋራዎች ግን አልሞት ባይ ተጋዳይ ነቄዎች ስለሆኑ ወድቀዉ እንዳይቀሩ መንግስትን ይፎካከራሉ፡፡
 
በጃንሆይ ዘመን ከነበሩት ሀገር ወዳድ መኳንንት መካከል በላይ ዘለቀ የጎጃሙ ጀግና ይገኝበታል፡፡ በላይ ዘለቀ ጠጅ ያሾምበት የነበረዉ ትልቅ ጋን ነበረዉ፡፡ይህ ጋን አሁን በምስራቅ ጎጃም ዞን ልዩ ስሙ ሶማ ከተባለ በርሃማ ቦታ ይገኛል፡፡ ሶማ በርሃ በላይ ዘለቀ ጣልያንን ሲወጋ መሽጎ የነበረበትና በመጨረሻም በጃንሆይ ወታደሮች ተላልፎ የተሰጠችበትእጉም ብሎ የተጠለለባትን ሰዉ አሳልፋ ሰጠች የቦታ ባንዳ ነች፡፡ ታድያ አሁን የበላይ ጋን ጠጅ የሚሾምበት ቀርቶ ጠጅ የሚጥልበት ሰዉ እንኳን ስለጠፋ የዞኑ ቅርስ ሆኖ የቱሪዝም መዳረሻ ለመሆን ተገደደ፡፡ይህን አይነት ታሪክስናገኝ ደግሞ ወደፊት ጠጅ ከነመጣሉ እንኳ እንዳይቀር ያሰጋል፡፡የነጃንሆይ ጋን የት ደርሶ ይሆን፣ የአጼ ሚኒሊክስ ዕንጦጦ ማርያምን ሲያስመርቁ ከጋን ተርፎ ጠጅ ያሾሙበት ጉድጓድ ምን ሆኖ ይሆን?

ጠጅን ስናስብ በጣም የሚያሳዝነዉ ነገር በእጅ ጣት በማትቆጠር እድሜ ዉስጥ  ከንጉስ ተላልፎ ለህዝብ መናኘቱ ከእልፍኝ ወጥቶ በገበያ ላይ መዋተቱ ነዉ፡፡ ጠጅ ቸርቻሪዎችም መቸርቸርያዎችም እንደ “ቸርች” ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተራቡ መምጣት ይዘዋል፡፡ እዚህ ላይ አንድ ጥያቄ እንድናነሳ ግድ ይለናል፡፡ ጠጅ ቤቶችና የጠጅ ደንበኞች በየሰፈሩ በየጉራንጉሩ የበዙት ለምንድን ነዉ? የሚል፡፡ እኔ ግን ጠጅ መሾሙ ቀርቶ መጣል ስለጀመረ ነዉ እላለሁ፡፡ የሚያሳስበዉ ነገር ግን ጠጅ መጣሉ አይደለም መሾሙ እንደቀረ መጣሉ ሲቆም ጠጅ ምን እንደሚሆን ነዉ፡፡
አዎ በነገስታ ዘመን ጠጅ አይጣልም ነበር፡፡ ይሾማል እንጅ፡፡ ለተራ ሰዉም አይሰጥም፡፡  የሚገርመዉ ጠጅ በተራ ሰዉ አለመጠጣቱ ሳይሆን በእንዲህ አይነት ሰዎች ቤት እንኳን አይሾምም ነበር፡፡ የሾመ ሰዉ ቢገኝ ቅጣት ነበረዉ፡፡ ጠጅ ለመሾም አንድ ሰዉ ማእረግ ያለዉ መሆን ነበረበት፡፡ አይ ጠጅ የነበረዉ ክብር ኖሯል አያ፡፡ እስኪ ይህን ታሪክ በማስረጃ እንይ፡፡ 

“………… See how our learnd and pious people lower themselves to an earthly king?” Berhan whispered into my ear. “one other thing Tewaney, Teji flows like water here but you and I can’t brew it at home, even if we wanted to, unless such a title such as Landowners or Kegnazmach or have fought in the flanks of a prince, or killed or captured enemy. People brew it secretly, though. If they are caught it will be confiscated and they may even face flogging, I find this truly detestable” (source Hiwot Teffera, Mine to Win 2016 p.138)
በግርድፉ ሲተረጎም 
…………..ብርሀን በጆሮየ እንዲህ ሲል አንሾካሾከ፡፡ ተመልከት የእኛ ህዝብ ራሱን ለምድራዊዉ ንጉስ እንዴት እንደሚያጎበድድ፡፡ ሌላኛዉ ተጨማሪ ነገር ተዋናይ፣ እዚህ ጠጅ እንደዉሃ ይፈሳል፣ እኔና አንተ ግን በቤታችን መሾም አንችልም፡፡ እንደዚህ አይነት ማእረግ ማለትም ቀኝ አዘማችነት፣ የመሬት ባላባትነት ከሌለን አልያም ከንጉስ ወታደር ጎን ተሰልፈን ጠላት ካልማረክን ወይም ካልገደልን ጠጅ መሾም ብንፈልግም አንችልም፡፡ ሰዎች ተደብቀዉ ጠጅ ይሾማሉ፡፡ ከተያዙ ግን ጠጁን ይቀማሉ እንዳዉም በጅራፍ ይገረፋሉ፡፡ በእዉነት ለመናገር ይህ ለእኔ አስከፊ ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡
ከ Mine to Win መጽሀፍ እንደምንረዳዉ ተዋናይ የቆሎ ተማሪ ሲሆን በ1857 የእድ ዉሃ አካባቢ ተወልዶ  በ1870ዎቹ በደብረ ወርቅ ማርያም ገዳም ፊደል፣ ንባብ እና ዜማ ተምሯል፡፡ ቀጥሎ ዋሸራ ማርያም በመሄድ ቅኔ ከሊቀ ሊቃዉንት ብርሀነ ሰረገላ ታየ እግር ስር እየተማረ በነበረበት ወቅት ቀኝአዝማች ሳህለማርያም የሚባል አንድ የመሬት ባላባት ድግስ ጠርቷቸዉ ጠጅ እንደ ዉሃ ሲጠጣ አስተዉሏል፡፡ በዚህ ወቅት አስተማሪዉ ሊቀ ሊቃዉንት ብርሀነ ስለጠጅ ምንነት በወቅቱ ምን እንደሚመስል ቅኔ በለመደዉ አፋቸዉ አሳምረዉ ለተማሪያቸዉ ተዋነይ ያስጨበጡት ቁም ነገር ለእኔም ጠጅ ዛሬ እንደተጣለ ያኔ እንዴት እንደተሾመ መጣጥፌ ትልቅ ማስረጃ ሆኖልኛል፡፡